ዓርብ 15 ጁላይ 2016

ርእደ-ሃሳብ

ጉዞዋን እንደምትጠነስስ፣ የማዕበል ጌሾ ቀንጥሳ
የፍዳ ባህር እንደምትገምስ፣ እንዳ'ንዲት ባለህልም ዓሣ ...

ልብን በሀሴት ሰንጥቃ
እስትንፋስ ከሥጋ ነጥቃ
ከእንቁ ልሳን ተወርውራ፣ ከክምር ጫጫታ መሃል
ነፍስን እንደምታክም፣ አንዳ'ንዲት ደመ-ሙሉ ቃል ...

ሲሻት የዘመን ፅልመት፣ በቅፅበት 'ምትደመስስ
ሲላት ያለምን እሳት፣ በ"እፍ"ታ 'ምትለኩስ
በጣቶች እቅፍ እንዳለች፣ እንዳ'ንዲት የክብሪት እንጨት ...

ላቅመ-መነገር ያልበቁ
ካልኳቸው ሺ'ጥፍ የላቁ
የህሊናዬን ግድግዳ፣ሳይታክቱ 'ሚደልቁ
እኒያ የብረት ኳሶች
እኒያ የሃሳብ ቦክሶች
ዉስጤን ፈንቅለው ቢወጡ
ምድርን ባንቀጠቀጡ
ፀሐይን ባቀለጡ።

ቅዳሜ 2 ጁላይ 2016

ግዴለም ይቅርብን

ግዴለም ይቅርብን ...
የመውደድ አዝመራ ማጨድ አልቻልንና
የቅጥፈት ቄጤማ መንቀል ተካንንና...
ግዴለም ይቅርብን...
ክህደት እምነት ይሁን
ጥላቻው ንፁህ ፍቅር
ሰማዩ ዝግ ጣሪያ
ሜዳው የግንብ አጥር።