ረቡዕ 27 ኦገስት 2014

እጅ የሰጠን

ከቶ አትጠየቅ "ለምን?" ትብለህ
ምን አሳቀቀህ ፣ ማን ሊሞግትህ
እንዳሻህ ጠርቅ ፣ ተርትር ነገርህን
የ "አሉ" ቱባ ፣ የወሬ ክምርህን
ሎጋ ምላስህን ፣ ሳለውና
በሾለው በኩል ፣ ሞርደውና
ቁረጥ ፣ ዘልዝል ፣ የወሬ ሻኛ
"ታመመ" ሲሉህ ፣ "ሞተ" በል ለእኛ
እኛ እንደሆንን፣
"ለምን?" ፣ "እንዴት?" 'ማይገደን
በ "መሰለኝ" ባህር የተወዘትን
የምይሞቀን ፣ የማይበርደን
ለምላስ ጀግና እጅ የሰጠን
ኩሩ የ "አሉ" ምርኮኞች ነን።

ማክሰኞ 5 ኦገስት 2014

መሃረቤን

"መሃረቤን ያያችሁ"
ብዬ ሳጫውታችሁ
"አላየንም" ላላችሁ
ሄድኩኝ እዛው ትቻችሁ።

መሃረብ ልሸምት ወጣሁ
ገበያዉን አዳረስሁ
ብዞር ከጫፍ እስከ ጫፍ
ተወዷል መሃረብ እንደ ጤፍ።

"ለምን?" ብዬ ብጠይቅ
ይመልሳል ባለሱቅ
መሀረብ የተወደደው
ዋጋው ሰማይ የነካው
ብልፅግና ኮርኩሮት፣
እንባው "አልቆምም!" ያለው
በሳቅ የሚያነባ፣
ሸማች ስለበዛ ነው።