ቅዳሜ 30 ጃንዋሪ 2016

የተቃርኖ ማማ

በሰጠምኩኝ መጠን ስንሳፈፍ
ከመናፍቅነት ገለባ ተበጥሬ ሳልፍ
ገላየ በልብ ከልብ ቀልጦ
ልቤ ከነፍስ ባህር ሰምጦ
ነፍሴ በፍቅር ቅመም ተላቁጦ
ገላዬ ማሳ ሆኖለት
ህመሜ ተዘራ ታጨደ
መድሃኒት ብዬ የዋጥኩት
ማዳበሪያ ሆኖለት ቀለደ።

ዋጋ

ሰርቆ ሳሚ ሲመጣ፣ ተይው በብላሽ ይላስሽ
የኔ ተራ ሲሆን ግን፣ ዋጋው ይናር ከንፈርሽ
ወሮ በላን ስትከሽው፣ ይቅር በይው ለምነትሽ
የኔ ወንጀል ሲሆን ግን፣ አይቀጡ ቅጣት ይኑርሽ።

አታሚ

ብቻዬን ከብቸኘት ስታገል
ፍርሃቴ ፍም አውጥቶ ሲንበለበል
ያ የስንብት አዋጅሽ
ያ የ "ደህና ሁን" ፍርድሽ
ልክ እንዳላዩት ሩቅ ሀገር
እንዳልገለጡት መፅሐፍ
እንዳልጠገኑት ሰባራ ልብ
እንዳላበሱት የንባ ዘለላ
ሰርክ የናፍቆት ጌሾ ነው፣
ዘሎ ፊጥ 'ሚል ከራሴ
ዞትር የቁጭት ጅራፍ ነው፣
ሰንበር አታሚ ከመንፈሴ።

ክፋቱ

ጨለማው ፍፁም ሳይፀልም
ብርሃኑም እጅግ ሳይለመልም
በተስፋ ነበልባል በእምነት
በጥርጣሬ ሰይፍ በፍርሃት
ስለመንደዱ ስለመድማቱ
ልብ ልብ አለማለቱ
ዘግይቶ ማወቅ ክፋቱ።

ኩ!

ቱግ ብዬ ተንተክትኬ
ከቆምኩበት ተፈትልኬ
ወረድኩኝ ከወንዛ ወንዙ
ሰከንኩኝ ካፍ ከገደፉ
ብለኩሰው አይበራ
ብደግፈው አይጠና
ብቆሰቁሰው ተዳፍኖ
ብኮተኩተው መንምኖ
ያሳብ ጠኔ ደልቆኝ
ያንጎል አፅሜን አድቅቆኝ
በደራሽ ድፍረት ተሞልቼ
ያሳብ ብስናዬን አግስቼ
ተወርውሬ ከዉሃው እንዳረፍኩ
እግዚኦ ከምኔው ሰጠምኩ
አበስኩ!
ገበርኩ!