ዓርብ 22 ኤፕሪል 2016

አይገርምሽም?

ድልድዩ ዋዣቂ፣
ካለት ሲያነክተን
ወንዙም ችኩል ደራሽ፣
ከግንድ ሲያላትመን
ባሕሩም ሞገደኛ፣
መርከብ ሲያስታቅፈን...
ህዋስሽ ህዋሴ፣
ነፍስሽና ነፍሴ፣
በዉዥንብር ናዳ፣ ሲልሙ ሲደቅቁ
አይገርምሽም ዉዴ፣
ቃልሽ ከቃሌ ጋር፣ እንዲህ መጣበቁ።

ምሽት ነበር

የኦሪዮን ክዋክብቱ፣
ርጌልና ቤቴልጌስ፣
ነጥተው ገዝፈው የቀሉበት
ምሽት ነበር፣ዉድ ምሽት
ዋጋው ካልማዝ ከ'ንቁ በላይ
ከፊቴና ከፊትሽ ላይ
ወዙ ደምቆ ፈክቶ ሚታይ።
ምሽት ነበር አይረሴ፣ ተስፋው ከማር የጣፈጠ
ለመግባባት ስንታገል፣ ሳንጨብጠው ያመለጠ።

አብረን ነበርን

ድልድይ ሆኖልሽ አልፈሽ፣ የኔ ሰፊ ትከሻ 
ያን የሰማይ ጉማጅ፣ ጣልሽው ባንዲት ጥቅሻ
እኔስ ምኔ ሞኝ ነው፣ ብድር ባየር መላሹ
በምድር አፈር ሳልቦካ፣ ነገን ዛሬ ቀያሹ 
እረፍት አልባ አይኖቼን፣ በትከሻሽ አሻግሬ 
ምርኮ አሰልፌ መጣሁ፣ ሳያገሳ ምንሽሬ።