ማክሰኞ 22 ጁላይ 2014

መራራቅ

ከ'ልፍ ማይሎች ልኬት ፣ ካድማስ የዘለለ  
ሰርክ ባንድነት ሆኖ እንዳ'ለመግባባት፣
 ምን መራራቅ አለ።

ሰኞ 14 ጁላይ 2014

በዚህ በጉድ አገር

በዚህ በጉድ አገር፣
መንገድ ላይ ማላመጥ ፣ ነውር በሆነበት
አደባባይ ቆሞ፣
እችግኝ ላይ መሽናት ፣ ማን ከልካይ አለበት።

በዚህ በጉድ አገር፣
በያደባባዩ፣
ባይነ-ህሊና ድሪያ ፣ ደም-ሥር ሲውጠረጠር
ስለወሲብ ማውጋት፣
በሹል ቃል አሳዶ ፣ ያስወጋል በነገር።

በዚህ በጉድ አገር፣
አንጀት ከድቶት ዝሎ ፣ ያገር ልጅ ሲያቃስት
ባርምሞ ምልከታ፣
ከንፈር መምጠጥ እንጂ ፣ ማን ከመጤፍ ቆጥሮት።

በዚህ በጉድ አገር፣
ጉልበተኛ ሲነጥቅ ፣ ላብ-አደር አፍኖ
መንገደኛው ያልፋል፣
በምን-ገዶኝ ግርዶሽ ፣ ማያዉን ሸፍኖ።

በዚህ በጉድ አገር፣
ጥራዝ-ነጠቅ ስያኝክ ፣ የቅልለትን ቅጠል
ትውልድ አሰልፎ፣
ያጠምቃል ሊህቁ ፣ የፍርሃትን ጠበል።

ዓርብ 11 ጁላይ 2014

ዋ!

ላ'የር ላይ መንበርሽ
ለዛፍ ላይ መኝታሽ
ዝናሩ የዲናር ፣ ጋሻው የብረት
ቋጥኝና አሸዋ በቋፍ ለያዙት
ዋ! ወዮሁለቱ
ዋ! ሰጋሁለቱ
የከሰለው ፍሞ፣
የከሰመው ግሞ፣
የተነሳ እንደሆን ፣ የሰደድ እሳቱ!

ፍቱን

የእውነት ዝናር ታጥቃ
የተስፋ ጦር ሰብቃ
ትእቢቷን አዉልቃ
ካንድ ራሷ ታርቃ
ተነስተው ፣ ተራጋጭ እግሮቿ፣
ተፈትተው ፣ ታሳሪ እግሮቼ፣
ያ'ፍ ልጓሜ ቢል-ላላ
እመሃል መንገድ ላይ፣
የሚታይ ለሚያይ፣
ቁብ ሰጥቶ ለሰማ፣
ዋይታው የሚሰማ፣
ለእርሷም የሚበጃት ፣ ለእኔም ያላደላ
ነፃነት የሚባል ፣ ነበር ፍቱን መላ።

ማክሰኞ 1 ጁላይ 2014

ተማፅኖ ወጎዳና

ለእናንተ ጎዳና ፣ ሰርክ መመላለሻ
ለእኔ ጎጆዬ ነው ፣ መረሳትን መርሻ
ለእናንተ መቆሚያ ፣ ወይ መተላለፊያ
ለእኔ ኑሮዬ ነው ፣ መገፋትን መግፊያ።

ላስመሳዩ ጓዴ

ለጥ ባለው ሜዳ ፣ ረግረግ ባልዞረበት፤
ከፊቴ እየቀደምክ ፣ መንገድ እንዳልመራክ፤
ድጥ እና ማጥ መሃል ፣ ሲገላበጥ ጎኔ፤
እንኳንስ ከፊቴ ፣ የለህም ከጎኔ።