ማክሰኞ 18 ኦገስት 2015

አንዳንድ ቀን

እንዳንድ ቀን አለ፣
ምናብን እንዳክናፍ ፣ በሰፊ አዘርግቶ
ብረር ብረር ሚል ፣ ከምድር አስነስቶ።

ደሞ አለ አንዳንድ ቀን፣
ቢሆንን ሚያስመኝ ዘላለም አንድ ቀን
ጠራርጎ የሚሸኝ የ'ላዌን ሰቀቀን።

አንዳንድ ቀን አለ፣
ሳይጠሩት አቤት ባይ
ሳይልኩት ወዴት ባይ
ይሉትን አይሰማ ፣ ቃላባይ እንዳ'ባይ።

ደሞ አለ አንዳንድ ቀን፣
የቀን ባለቅኔ
በቆፈን ቆርብተህ ፣ ተቆራምተህ ሲያይህ
ሳጥን ሙሉ እርዛት፣ ደራርቦ ሚያለብስህ
ሌማት ሙሉ ጠኔ፣ ፈትፍቶ ሚያጎርስህ
እንጀትክን ሊያርስህ።

ረቡዕ 12 ኦገስት 2015

ሕይወት እንቆቅልሽ

ጠረኗ አይደገም ፣ ሁሌ አዲስ ላፍንጫ
ቀለሟ አይጨበጥ ፣ ነጭ ጥቁር ግራጫ
ሲለቋት እንክትክት ፣ ሲይዟት ሙልጭልጭ
ሲቀርቧት እርብትብት ፣ ሲርቋት ብልጭልጭ
ጀምበር ስትፈነጥቅ ፣ በፍካት ማለዳ
ሕይወት እንቆቅልሽ ፣ ሰርካ'ዲስ እንግዳ።

ማክሰኞ 11 ኦገስት 2015

ተለመኑኝ

በብቸኝነት ቋቅታ ነው ፣ ከየልባችሁ መብቀሌ
በኗሪነታችሁ ትንሣኤ ነው ፣ ሞትን አንቄ መግደሌ
ከልቡናችሁ ኮትኩቱኝ ፣ እንዳልጠወልግ እንዳልደርቅ
ፍቅርን "እ..ፍ" በሉብኝ ፣ እንድለመልም እንድፀድቅ።

ማክሰኞ 4 ኦገስት 2015

የልጅ ምኞት

ዋ...ልጅነት ችግኝነት
ለመፅደቅ ችኩልነት
በዘልማድ ምኞት ክንፈት
ንፁህ የሩቅ ሕልመኝነት
በድንገት ሀኪምነት (ድዌ ሊታከም)
በቅፅበት ማንዲስነት (ሊቃና ጥምም)
ቀና ብሎ አብራሪነት(ከንስር ሊቀደም)...
ዛሬ በብስለት ዋዜማ
የሕልሜን ድምፅ ስሰማ
ራሱን አድሷል ምኞቴ
ቢሳካልኝ ቢቀናኝ ፣ ብሆን ሲሶው ያ'ባቴ
ብታደለው ብመረጥ ፣ ብሆን ሩቧ የ'ናቴ
በሰውነቴ።

እሑድ 2 ኦገስት 2015

የተስያት ቆፈን

ከላይ የጠል ቁጣ
ከታች ምድር ቀልጣ
ላቤን ከጅማቴ ጠልቄ ቀዳለሁ
ከ'ሷ ጀርባ ቆሜ ተራ ጠብቃለሁ...
አርሳው ወይ ሸምታው ያልለየለት ጠጉሯ፣
መቃ አንገቷን ታ'ኮ
ችቦ'ገቧን አንቆ
ጉብታዉን ተንተርሶ
ሸለቆውን ባይኑ ልሶ
አደናቀፋት ስል ፣ አጋደማት ጠልፎ
ሽቅብ ይታዘባል ፣ ከቋንጃዋ አርፎ...
ሹክ ያልኳት ይመስል፣
ወደ ጎምዢው ፊቴ ፣ ፊቷን ብታዞረው
ቅፅበታዊ ቆፈን ፣ ጅስሚየን ወረረው...
ጉድ እኮ ነው!
ያጠመቀኝ ላቤ ወደ ላይ ተነነ?
የጠሃይዋ ቁጣ ከምኔው መነነ?
አሁን በዚህ ፍጥነት ፣ ተፈጥሮ ተዛባ?
ወይስ እዚሁ ቆሜ ፣ ክረምት ዘሎ ገባ?

ከአዕላፍ በስቲያ

ከልክነት ልኬት ልቆ
ከመሳሳት ስቀት ርቆ
ትናንትና ከሽልቡ ነቅቶ
ዛሬ ባንኖ ተንጠራርቶ
ነገ ቀድሞ ካልተኛበት
የቀን ውድቅት ካልሆነበት
ፍቅር ጥንቡን ካልጣለበት
ቆሜያለሁኝ ከፊት ጀርባ
ከኔና አንቺ የሐቅ አምባ።

ገደብ

ከውቅያኖስ መሃል፣
ከተንሳፈፍንበት ባ'ሴት ሰረገላ
አኑሬልሻለሁ የንባዬን ዘላላ
ዉሃውን አስሰሽ ያገኘሽው ለታ
ያኔ ነው ስስቴ ናፍቆቴ ሚገታ።