ማክሰኞ 29 ኤፕሪል 2014

ሰሚ ማጣት

አንገቴ አይል ቀና ፣ እንዳምናው ዘንድሮ፤
በደም መጣጭ ተባይ ፣ ጫንቃዬ ተወሮ።
ከላዬ አሽቀንጥሬ ፣ አላፈርጠው ነገር፤
እጄ ተጠፍሯል ፣ ግራው ከቀኙ ጋር።
እንዳልደባልቀው ፣ መንደሩን በሩምታ፤
ልጉሙ ልሳኔ ፣ ነጥፏል ለኡኡታ።
የጆሮ ኩሊ እንጂ ፣ ሰሚ በሌለበት፤
በግፍ አዳራሽ ዉስጥ ፣ ጥግ ይዤ በትዝብት፤
በዝምታዬ ፍም ፣ አቀልጣለሁ ጩኸት።

ዓርብ 25 ኤፕሪል 2014

ያገሬ ባላገር

"ቀለም የዘለቀኝ" - ብለህ ካልተኮፈስህ
ካፈር መደቡ ላይ - አብረህ ከተሰየምህ
የከተበልህን - እንቶኔ አሰማምሮ
የለቃቀምከውን  - ዙረህ እንደ ጭራሮ
ወረቀት ከብእር - የግድ ሳያዋድድ
ከህሊናው ማህደር  - ይቀዳዋል ለጉድ።

ትረካ በእጁ  -  ማዋዛት በደጁ
ምን ብዥታ ቢብስ - በንቅልፍ ቢያንጎላጁ
የኋሊት ለማየት - አይኖቹ አያረጁ።

"እኔ አውቅልህ" ብሎ - ባዕድ የጋተህን
"ወገኔ" ምትለው - ያወላገደውን
የታሪክ ጠቃሚው  - የደራረተውን
ቀንና ሰዓቱ - ሳይዛነፍ ውሉ
ሳይለቅ ቀለሙ - ሳይደበዝዝ ምስሉ
በትዝታ ፈረስ  - በዘመን ኮርቻ
አፈናጦ ሚያደርስ - ከኩነት ዳርቻ
ላገሬ ባላገር አጣሁለት አቻ።

ረቡዕ 23 ኤፕሪል 2014

ጎብጦ

እንዴት ቀና ልበል ፣ አንደምንስ ብዬ፤
በፋታ-አልባ ሸክም ፣ ጎብጦ ትከሻዬ።

ጠራቢ እጆች

በነኛ ዉብ እጆች ፣ በድንጋይ ጠረባ
ያክሱም-ላሊበላ ፣ ጥበብ ተገነባ።
የኚህን ድንቅ እጆች ፣ አሻራ መርምረው
ፀሐይ 'ማይከልል - ዝናብ 'ማያስጠልል፣ ቆባቸውን ደፍተው
በተርታ ተሰጥተው በየ-ምን-ገዱ ላይ
ዛሬ ቀንም እጆች ይጠርባሉ ድንጋይ።

በላቡ

የመንደራችን ሹም ፣ መኳኳሉ በዛ
ሁሉም አያወቀው ፣ በላቡ እንደወዛ።

ገበያው

ሸቀጡ ለጉድ ነው ፣ ገበያውም ደርቷል 
ዋጋው በማይጎዳ ፣ ባገር ሻጭ ተሞልል።

አትዙር!

ወደ ኃላ አትዙር! ወደፊት አተኩር!
ትይኝ የነበረው ፣ ናላዬ እስኪዞር፤
ያመጣንን መንገድ ፣ እንድረሳው ነበር?
ይብላኝ እንጂ ላንቺ፣ እኔስ አገኘሁት፤
ጥምዝምዙን መንገድ ፣ መልሼ አሰመርሁት፤
የጀርባሽ ነፀብራቅ ፣ በፈጠረው ጨረር፤
ወለል ብሎ ታየኝ ፣ እጥፋቱ ጭምር።

ሰኞ 21 ኤፕሪል 2014

ገዥና ሻጭ

የጥንቱ ነጋዴ ፣ ስንፍናው ላሳር ነው፤
መሸጥ አይችልበት ፣ መግዛት ካባቱ ነው።
የዘመኑ ጮሌ ፣ ብልጥ ነው ጨላጣ፤
መግዛቱ ሳያንሰው ፣ በንጣቂ ረብጣ፤
አንደ'ዜ በጥቅል ፣ ሌላ'ዜ ቆንጥሮ፤
ባ'ራጣ ይሸጣል ፣ ወለድ ተደራድሮ።

ዓርብ 18 ኤፕሪል 2014

ተነድፏል

አትደነቁ ቢያወራ፣
ቆሞ ከጥላው ጋራ፤
አይጭነቃችሁ ቢባንን፣
ከምትጣፍጥ ሰመመን፤
አይግረማችሁ ቢያውካካ፣
በዱር በገደል በጫካ፤
አትሳቀቁ በርቃኑ፣
ገላው ቢከዳው ሽፋኑ፤
አትሳለቁ ቢያደናቅፈው፣
የ'ውነት ገመድ ቢጠልፈው፤  
ከምንይሉኛል ተኳርፎ፣
ባይለቄ ልክፍት ተለክፏል።
በሀቅ ትንኝ ተነድፏል።

አባልቶ

በጠኔ ጠውልገን ፣ ባየን ጊዜ አዘነ 
አዝኖም አልቦዘነ ፣ ሊያጠግበን ወጠነ
እጃችንን ታጠብን ፣ እጆቹን ታጠበ
ከሞላው ገበታ ፣ ሊያባላን ቀረበ
ካጥንት ከመረቁ ፣ እያሳለፈልን 
ከጠላ ከጠጁ ፣ ሲያንቆረቁርልን 
እስክንሰክር ፣ አጣጥቶ
እስክንጠግብ ፣ አባልቶ
እርሱ አሸለበ፣ 
እኛን እንቅልፍ ነስቶ።

ማክሰኞ 15 ኤፕሪል 2014

አበረታኝ

ወፌ ቆመች ከማለቴ
ሲያርቋት ምርኩዜን ከፊቴ
ቀና ስል ላይ ከፍታ
በኩርኩም አናቴ ሲመታ  
ስጀምር መሄድ መራመድ
ሲያረጉት እግሬን ሽምድምድ
እንደለመዱት ሊያመክኑት
መንፈሴን ሲቀጠቅጡት
እንኳንስ ተሰብሮ ሊያሳጣኝ
ካለት ፀንቶ አበረታኝ።

እሑድ 13 ኤፕሪል 2014

አንቺ'ኮ

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
ሙሉ ጉባኤ ሲስቅልኝ
ፈገግታዬን ሲያፀድክልኝ፣    
ሰርስረሽና ጎርጉረሽ
ልቅም አርገሽ አበጥረሽ
አንግዋለሽና አንጥረሽ ፣
ከሚያስንቅ ግዙፍ ጋራ    
ከክምር ፈገግታዬ ተራ
ያዘኔን እሾህ ትመዣለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
ተሰፍቶ ጥርሴ ከከንፈር
ወይ አልናገር ወይ አልጋገር
"ጋግርታሙ!" ሲለኝ አገር፣
ሳልተነፍስ ሽራፊ ቃል
ጠጠር ከልሳኔ ሳልወረውር፣
ፀጥ ያለዉን ፀጥታዬን
ልቤ ላይ ጆሮሽን ደቅነሽ
የጥሞና አደማጬ ነሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
እሳት ለብሼ እሳት ጎርሼ
ሳስቸግር ለያዥ ለገራዥ፣
ደሜ ሞቆ ሲያተኩስ
ቀረርቶዬ ሞልቶ ሲፈስ፣  
ከንዴቴ ነበልባል ወስደሽ
የእሳት ደመና ሰርተሽ  
የፍቅር ዶፍ ታዘንቢያለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
በስስት ሲቃ ሳቃስት
አይኔ ከማዶ ሲቃትት፣
ጨረቃን በምናቤ ሳቅፍ
ክዋክብት ከሰማይ ሳረግፍ፣
ስሜት ሲያረገኝ ወፈፍ
ከንፈሬ ከንፈርሽን አፈፍ፣
በሃሴት ቀልጬ ስከንፍ
በንዝረት ባህር ስንሳፈፍ፣      
ስትዳባብሽኝ ባይኖችሽ
የናፍቆትን ጉም በትነሽ
የርካታ ጠበል ትረጫለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።

ምነዋ ጣይቱ?

ፍጥረት አይኑን ገልጦ
ግራ ቀኙን ቃኝቶ
ተንጠራርቶ ተጠራርቶ፣
ምድር ፊቷን አፍክታ
ቆፈኗን በጮራ ተክታ፣
ምኞት ከተስፋ ሰንቆ
አንጀቱን ቋጥሮ አጥብቆ፣
ዱር ገደሉን ሊያቀና
ወገን ባለ ደፋ-ቀና፣
ባንቺ በጣይ'ቱ
በብርሃን ለጋሲ'ቱ፣
ስታሞቂን በፈገግን
ስታበስይን በሞከክን
እያረርንም እንደሳቅን
እያከሰልሽ አሳመድሽን።
ግን ለምን ጣይ'ቱ?!
ብርሃን ለጋሲ'ቱ!
አንፀባራቂ'ቱ!

ዓርብ 11 ኤፕሪል 2014

አዋራጄ

ወጥቼ አቀበቱን ፣ ያላንዳች እገዛ
ቁልቁል ስንደረደር ፣ አዋራጄ በዛ።

አስባ'ለሁ

ሃሳብ አወጣ'ለሁ፣
እሸከመዋ'ለሁ፣
ሃሳብ አወርዳ'ለሁ፣
ባሳብ እወጣ'ለሁ፣
እንጠላ-ጠላ'ለሁ፣
እወዛ-ወዛ'ለሁ፣
እንሸራተታ'ለሁ፣
ባሳብ እወርዳ'ለሁ፣
ሃሳብ አስባ'ለሁ።

ረቡዕ 9 ኤፕሪል 2014

ይመስገነው አለን

ይመስገነው አለን ፣
ቁጥርን እንደ ቁርጥ
ቆርጠን እየበላን፣

ይመስገነው አለን ፣
እምባን እንደ አምቦውሃ
ቀድተን እየጠጣን፣

ይመስገነው አለን ፣
ጨለማ እንደ ፋኖስ
ዞትር እያበራን፣

ይመስገነው አለን ፣
ቁጭት እንደ ባቡር
ተሳፍረን ሽው እያልን፣

ይመስገነው አለን ፣
እጅግ እንደረቅቀን
እንደተንደላቀቅን
እየሌለን አለን።

መጥዋቹ

አዛኝ የሚመስለው
ከንፈር የሚመጠው
የፀዳ የነጣ ኩታ የሚለብሰው
ለጥድቅ እጅ መንሻ እጁ የሚፈታው ፣
ይሄ እልፍ አሕዛብ ይሄ እልፍ አማኝ
የሚርመሰመሰው ባለፍኩ ባገደምኩኝ
ቤሳ ሲጥል እንጂ ሲሰጥ አላየሁኝ።

NB: Inspired by Bewketu Seyoum's "The road to nowhere" on Modern Poetry in Translation

ማክሰኞ 8 ኤፕሪል 2014

እ-ና-ሸ/ቸ-ን-ፋ-ለ-ን!

ያ ጓዴና እኔ፣ ፊትለፊት ተያየን
"ወዴት ነህ ? "ተባባልን
ኢላማ ግባችን እንድነቱን አወቅን።

ፅዋችንን ሞልተነው
ለድላችን ከፍ አርገነው
አጋጭተንም ቀመስነው።

የጉምዝዝ ጣፋጭ ነው
ባንዳፍታም ፉት አልነው
ለጥቀን ጨ...ለ...ጥ...ነ...ው።

አልኩኝ በሞቅታ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ቀጠለና ጓዴም ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ስንሸልል ፣ ስንፎልል ፣ ሳይገድረን እንቅልፍ
አንዳች ድምፅ ሰማን እሳት 'ሚያርከፈክፍ።

የሰደድ እሳቱ ዘንቦ ... ዘንቦ ... ዘንቦ!
ቡቃያውን መርጦ በቀይ ጎርፍ አጥቦ
የረገፈው ረግፎ ፣ የተረፈው ተርፎ
የደለል ሙላቱ አንጉዋሎ አንሳፎ
እኔም ተ--ን-ፌ ፣ ጓዴም ተ--ን-ፎ
ያለያየን መንገድ ባንድ ላይ ጠቅሎን
በስደት ታንኳ ላይ ዳግም አገናኘን።

ያ ጓዴና እኔ ፣ ዛሬም አልተማርን
ያ የቃል እባጩ ፣ ሶንኮፉ አልወጣልን
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
እያልን ዛሬም "አለን"።

ሐሙስ 3 ኤፕሪል 2014

የግጥም-ጥም

በምናብ መገለጥ ተጋግሮ
በብርሃን ሰይፍ ካልተቆረሰ፣

በፅናት መቀነት ጠብቆ
ባንጀት ካንጀት ካልተቋጠረ፣

በመራር ያሞት ከረጢት
በእውነት ካልተሰተረ፣

በሃሳብ እንዝርት ሹሮ
በስሜት ቀመር ተዳውሮ
በተቡ ቃላት ካልተሸመነ፣

በዉበት ጥለት ተቋጭቶ
በሕብረ-ቀለም ካልተሸለመ...

ካንገት በላይ ተጠምቆ
ቅራሪ ስንኝ ቢቀዳም፣
ምላስን ከማራስ አልፎ
የግጥምን ጥም አይቆርጥም።

ማክሰኞ 1 ኤፕሪል 2014

እነርሱ ለእርሱ

ያረገዝውን እያማጡ
ያማጠውን እየወለዱ
የወለደውን እየሳሙ
ያሳደገውን እየዳሩ
የሞተበትን እየቀበሩ
ሙት-አመት እየዘከሩ
በምስለ-እርሱ ሲኖሩ፣
እርሱ ሲፈልግ እርሱን
ስጋው ቢሸኛት ነፍሱን፣
ያልሆናቸው ግን የሆኑት
ጨክነው ሜዳ ላይ ሳይጥሉት፣
በእልፍ ፍራንክ በተገዛ
በተሰራ ከርጥብ ዋንዛ
በልኩ ጎጆ ቀለሱና
ያፈር ካባ ደረቡና
አስሸለቡት ላይል ቀና።