ማክሰኞ 8 ኤፕሪል 2014

እ-ና-ሸ/ቸ-ን-ፋ-ለ-ን!

ያ ጓዴና እኔ፣ ፊትለፊት ተያየን
"ወዴት ነህ ? "ተባባልን
ኢላማ ግባችን እንድነቱን አወቅን።

ፅዋችንን ሞልተነው
ለድላችን ከፍ አርገነው
አጋጭተንም ቀመስነው።

የጉምዝዝ ጣፋጭ ነው
ባንዳፍታም ፉት አልነው
ለጥቀን ጨ...ለ...ጥ...ነ...ው።

አልኩኝ በሞቅታ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ቀጠለና ጓዴም ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ስንሸልል ፣ ስንፎልል ፣ ሳይገድረን እንቅልፍ
አንዳች ድምፅ ሰማን እሳት 'ሚያርከፈክፍ።

የሰደድ እሳቱ ዘንቦ ... ዘንቦ ... ዘንቦ!
ቡቃያውን መርጦ በቀይ ጎርፍ አጥቦ
የረገፈው ረግፎ ፣ የተረፈው ተርፎ
የደለል ሙላቱ አንጉዋሎ አንሳፎ
እኔም ተ--ን-ፌ ፣ ጓዴም ተ--ን-ፎ
ያለያየን መንገድ ባንድ ላይ ጠቅሎን
በስደት ታንኳ ላይ ዳግም አገናኘን።

ያ ጓዴና እኔ ፣ ዛሬም አልተማርን
ያ የቃል እባጩ ፣ ሶንኮፉ አልወጣልን
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
እያልን ዛሬም "አለን"።

ምንም አስተያየቶች የሉም:

አስተያየት ይለጥፉ