ማክሰኞ 26 ዲሴምበር 2017

ለብርቱ ትከሾች እጅ መንሻ

"ወጡ ቀለም ሆኖ እንጀራው ብራና
ይድረሰኝ ደብዳቤ ተርቢያለሁና"
ብሉ እንዳልማለደ
ንፋስን አማላጅ፣
ጨረቃን አዋላጅ፣
አርጎ እንዳልነጎደ
ገብሬ ኢልማ ደስታ እንደዘበት ሄደ
ኦክላሆማ ሜዳን ቤት አርጎት ለመደ።

ከዴህሊ እስከ ሎንዶን
ከይፋት እስከ ዋሽንግቶን
ባሻ አሸብር ባለ ቧልቱ
ደማሙ ብእረኛ አብዬ መንግስቱ
ያለ ፕሮብሌም አርፎ መተኛቱ!

ዮሐንስም ሄደ፣ ሰፊ አድማሱን አስታቅፎን
"እስኪ እናንተ ጎዱች ተጠየቁ" ብሎን
በብቸኝነት ነበልባል እንደነደደ
ቅኔው ይፋቴ ዳኛቸዉም ነጎደ
ኡኡታ አሮበት "እምቧ በሉ" እያለ
የጉራማይሌ ሕልሙን፣ ቁጭት እየፈተለ
ዮናስ በኩርምት ሞቱ እያሳለው ተከተለ
"እግዚያአብሔር ትመስን፣ ክብሯ ይስፋ" እንዳለ።

ደበበ በምናቡ ስይፍ ክትፎኛ ተካትፎ
ገሞራው በረከትን ሼጣንኛ ተራግሞ
የዜሮን ቁጥርነት ከአልፋው ሞግቶ
እውነት ለሚያንቀው አገጭ ይዞ ግቶ
ከዑራኤል ዳገት ሽቅብ እየቃኘን
"እኔም እንደናንተ ሕያው ነበርኩ" አለን።

አያ ሙሌም ምህላዉን ታክቶ
አጅሬው ከመንበሩ መኖሩን ሞግቶ
ክልትው አለ ብቻዉን፣ አዘመራውን እንደነዛ
በሱ የደም ጠብታ፣ የስንቱን ግንባር ሊያወዛ።

ከአባ ገዳ ኢልማ ገልማ
የማይድን በሽታ ነፍሱ አስታማ
ከመርካቶ እስከ ኮምፔሽታቶ
ከመቅደላ እስከ ላሊበላ
ከኢዞፕ እስከ ኢቶፕ
ከሐምሌት እስከ ኦቴሎ
ያ ፀጋዬ ማሎ ማሎ።

ከጩታ እስከ ፓሪስ
ከዊንጌት እስከ ምኒያፖሊስ
ልጅነቱን አነባብሮ
ዘበት እልፊቱን ተሻግሮ
ለብስለት ወዜማ ተቃጥሮ
ወለልቱው ስሎሞን ላይመተር ረዘመ
በዉርጭማ ሰማይ ላይጨበጥ ተመመ።

ዓርብ 1 ዲሴምበር 2017

ሀሴት-ወለድ ሙግት

ድንቅነትሽ እጡብ ድንቅ
ጨቅላ ፍጡር የሚያስቦርቅ
ነፀብራቅሽ ዘንጉ ረዥም
ከሰሜን ዋልታ አንስቶ፣
እስካንታርክቲካ የሚያንፀባርቅ
ያይኖችሽ ጦር ሰበቃ
ከሞት ታናሽ ወንድም፣
ብርሌ ነፍስ የሚያነቃ
ፈገግታሽ ላድማስ ቦግታው
የደመናትን መንጋ፣ ከሰማይ ላይ የሚመታው
ካለው፣ ካልነበረው
ከሌለው፣ ከሚኖረው
ተጣጥተን፣ ተፋልገን
ተራርበን፣ ተጣግበን
ዉል አልባ ተጣልፈን
አይፈቱት ተቋልፈን
ነግቶ እማኝ እንዳይሆን፣ አንሶላ ቀደድን
ክዋክብት ተጋፈን፣ በሸንጎ ቀለድን።

ተጠየቅ እረኛ

ጠረቃሁ ለማታውቅ፣ ብትጠጣ ብትበላ
ለዚህች ለራስ ወዳድ፣ ላንዲት ከርስ ተድላ
ከገል ለተበጀች፣ ቁንፅል የዕድሜ ጀምበር
ዋስትና ለሌላት፣ ከሴኮንድ በኋላ እንደማትሰበር
ስንደዶ ቀንጥሰን፣ የገመድነው ጅራፍ
መልሶ ገረፈን፣ ባጦዝነው ሺህ እጥፍ።

እኔን ሲዳኝ እኔ

አህያን ከጅብ ሳጣጥም
አይጥን ከድመት ሳሳስም
ዲስኩሬ በዉድ ሲያዋድድ
ፍም እሳትን ከደረቅ ጭድ
ልሣኔ ፈልጎ አቃርቦ
አራምባዉን ከቆቦ
ግና ምን አገኘኝ፣ ጎደልኩት ከራሴ
ደርሶ የሚከዳኝ፣ ጥሬ ቆይ ምላሴ።

ሰኞ 30 ኦክቶበር 2017

አርዶ አደሮች ሆይ

ባሩድ እንደጠበል፣ በጅምላ እየረጩ
አረም ለማቆየት፣ ቡቃያ እየቀጩ
በደም ቀይ ምንጣፍ፣ ዛሬን ቢራመዱ
ነገ ሸንጎ 'ሚቀርብ፣ ዶሴ ነው መንገዱ።

ቢሆንም ባይሆንም

የህልማለም ድግስ፣
ህላዌን አንጥሮ፣ ቢያጠጣም ቅቤ
አዋዝቶ ቢያጎርስም፣ ክትፎን ከአይቤ
ሰው ምኑ ሞኝ ነው፣
ገር ሕልሙን ተማምኖ፣ አይተኛ በራብ-ጥም
ጉምዥት ሳይጎነጭ፣ ተስፋ ሳይቆረጥም።

እኔን ሲዳኝ እኔ

አህያን ከጅብ ሳጣጥም
አይጥን ከድመት ሳሳስም
ዲስኩሬ በዉድ ሲያዋድድ
ፍም እሳትን ከደረቅ ጭድ
ልሣኔ ፈልጎ አቃርቦ
አራምባዉን ከቆቦ
ግና ምን አገኘኝ፣ ጎደልኩት ከራሴ
ደርሶ የሚከዳኝ፣ ጥሬ ቆይ ምላሴ።

ዉሃ ወቀጣ

ልቦና ታውሮ፣ አይን ሲያክል ጨረቃ
ሳሙና ፈልሳፊው፣ ሲሆን ታጥቦ ጭቃ
ማሰብ ምን ሊረባ፣ መፅዳትስ ለምኔ
ተጨምቆ ላይወጣ፣ ፅድቅ ከኩነኔ።

ረቡዕ 25 ኦክቶበር 2017

በጫጉላ ጨረቃ

የናፍቆትን ጋራ፣ አሟምተሽ ስታልፊ
የትዝታን ግርዶሽ፣ ገላልጠሽ ስትገፊ
ድካምሽን ለማከም፣ በቀኝሽ ስታርፊ
የእንቅልፍ መንኩራኩር፣ ይዞሽ ሲመነጠቅ
የህልም ሰረገላ፣ አሳፍሮሽ ሲነጠቅ
ከማረፊያሽ ልቤ፣ ሰገነት ቁጭ እንዳልሽ
ያ'እዋፍ ሕብረ-ዜማ፣ ቀስቅሶ ካነቃሽ
ይልቅ ጆሮ ስጪ፣ ለማለዳው ዜማ
አዋጅ ይዟልና፣
በኔ የሚነገር፣ ባንቺ የሚሰማ።

ልፋ ያለው ምናብ

ልቦና ታውሮ፣ አይን ሲያክል ጨረቃ
ሳሙና ፈልሳፊው፣ ሲሆን ታጥቦ ጭቃ
ማሰብ ምን ሊረባ፣ መፅዳትስ ለምኔ
ተጨምቆ ላይወጣ፣ ፅድቅ ከኩነኔ።

እሑድ 10 ሴፕቴምበር 2017

ቤት የለኝምና

እደጅ እንዳላድር
ኮከብ እንዳልቆጥር

ከሩቅ አብረቅራቂ፣
አብሪ - ተወርዋሪ፣ ኮከቦች አለቁ
ከሰማይ ላይ ወልቀው፣ ካፈር ተጠለቁ

ምድር ባደይ ኮከብ፣ ተኩላ ቢያዩ
ታምራት አውጀው፣ ዓሶች በረገጉ
ዉቅያኖስ እንግተው፣ ከንፌ-አውጪኝ አረጉ

ዉሃውና ዓሳው፣ ሰማይ ከከተሙ
ክዋክብት አምረው፣ ቁልቁል ከተመሙ
ከዘመን ጋር ዘምኗል፣ ኩርማንን ፍለጋ
ሽቅብ አያንጋጠጥን፣ መረብ እንዘርጋ።

ቅዳሜ 2 ሴፕቴምበር 2017

እሳትና ዉሃ

እብሪት እንደዝናር፣ አጥብቀው በሚያስሩ
ክብሪት እንደክራር፣ በሚደረድሩ
በእፍባዮች ምድር፣ በቆስቋሾች ዓለም
መሆንህን ረስተህ፣ አንድ ዘለላ ፍም
የኔን ጠብታነት፣ ቁልቁል እያየሃት
መሆንህን ነገርከኝ፣ የማትከስም እሳት

እድሜ ለዝናቡ፣
አጭዶ ለሚወቃው፣ የዶፉን አዝመራ
ተግቶ ለሚሞላው፣ የውቅያኖስ ጎተራ
ምስጋና ለንፋስ፣
ሳይታክት ለሚሰጥ፣
ለጡዘትህ ቤንዚን
ለእብደትህ እስትንፋስ
 
ባንድነት ለመጥፋት፣ እንዳልተፋለግን
እልፎች እንዲፀድቁ፣ አብረን ጠወለግን።

ረቡዕ 30 ኦገስት 2017

ባንድ አምባ

ነጋ፣
ቀን ሌትን ፈንግሎ፣ ባምባው ሊገንበት 
ሰው ሕልሙን ሊራመድ፣ ነቃ ከተኛበት 
ሲማስን - ሲኳትን፣ አይተጉ ሲተጋ
ላልጨበጠው አልፋ፣ ኦሜጋ ፍለጋ
መሸ፣
ፍጥረት አፏሸከ፣ አይዘጉት አዛጋ
ሁሉም ተከተተ፣ ሁሉም በሩን ዘጋ
ሲያፈጥ እንዳልዋለ፣ ቀን አይኑን ከደነ
በእንቅልፍ ቡልኮ፣ መስሚያዉን ሸፈነ 

ሌት ሆይ ባለተራው፣ አምባገነን ሆነ።

ረቡዕ 16 ኦገስት 2017

ክቡራን ሸኝዎች

ሕይወት ሸኝታችሁ፣ ሃውልት ልታኖሩ
በእድሩ ጥሩንባ፣ ቀበቶ እምታስሩ
ለሂያጅ መታወሻ
ለሞቱ ማርከሻ
ብረት ስታቀልጡ
አለት ስትፈልጡ
አፈር ስታቦኑ
አሸዋ ስትዘግኑ
ነፍሱን እንዲደላት፣ በአፀደ-ገነት
ስትገቡ ሱባኤ፣ በደብር ሰገነት
ይልቅ አንድ ነገር፣ ጠይቁ መርምሩ
የት ጋር እንደሆነ፣
ቀሪዉን ከሂያጁ፣ መለያ መስመሩ።

ሰኞ 17 ጁላይ 2017

አእምሮ ከሰማይ ይሰፋል

አእምሮ ከሰማይ ይሰፋል፣
መሳ ለመሳ ቢቀመጡ
አንዱ ሌላዉን ሳያቅማማ መሰልቀጡ።
አእምሮ ከባህር ይጠልቃል፣
መልክ ለመልክ ቢነፃፀሩ
ባልዲ ዉሃ በስፖንጅ እንዲመጠጥ
እንዱ በሌላው ባፍታ ይጨለጥ።
ያ'እምሮ ሚዛን ልኬቱ
አቻ ነው ከፈጣሪው ከጠበብቱ
እፍኝ ለእፍኝ መዝኖ
ኪሎ ለኪሎ ተምኖ
አንዱን ከሌላው መነጠል
ድምፀትን ከድምፅ እንደመፍተል።
--------------
መነሻ: "The Brain -is wider than the Sky" -- Emily Dickinson

ዓርብ 7 ጁላይ 2017

ነገን

ቅንጣት ሳይጠብብን፣ የጥበት ስፋቱ
ከቶ ሳይጋርደን፣ የፅልመት ፍካቱ
ወትሮ ሳያንስብን፣ የማነስ ግዝፈቱ
ሞልቶ ሳይፈስብን፣ የባዶ ሙላቱ
ከሃሴት ከረጢት፣ ስሜት ተሰድሮ
ከምናብ ጋን ሙላት፣ ክዳን ተስፈንጥሮ
የሀቅን ወለላ፣ ጨለጥናት ባንዳፍታ
የኋሊት እያየን፣ ነገን በትዝታ።

ሐሙስ 20 ኤፕሪል 2017

ተፈጥረሃልና

በእኔና አንተ ምድር፣
ሆነህ አትፈጠር፣ ችግኝ ባለ ተስፋ
ከቶ ብቅ አትበል፣ በኮትኳች ልትፋፋ።
ባርባ ቀን እድልህ፣ ብታመልጥ ከ'ርግጫ
በመርፌ ቀዳዳ፣ ብትሾልክ ከድፍጥጫ
ዋ ሽተህ፣
ዋ ብትል፣
የሽንት ጎርፍ ነው፣ የጥምህ መቁረጫ።

ይህን ሁሉ ችለህ፣
በጥቂት ኮትኳቾች፣ ጠንተህ ብትፀድቅ
በፀሐይ እስትንፋስ፣ ብትወዛ ብትደምቅ
አንሰራራሁ እንዳልክ፣ አየሁ አዲስ ዓለም
ቅጠሎችህ ረግፈው፣ ቅርንጫፍህ የለም።

አይችሉትን ችለህ፣
ዳግመኛ ሥር ሰደህ፣
መክሰም መጠውለግን፣ ቀንጣት ሳትፈራ
ግንድህ አቆጥቁጦ፣ ፍሬ ስታፈራ
እልፍ ነው ቀጣፊህ፣ በሰልፍ በተራ።

ከቅጥፈቱ ናዳ፣ አፅምህን አትርፈህ
ከራስ በስትያ ስሌት፣ ዋርካነት አልመህ
ባሸለበች ፀሐይ፣ በነቃች ጨረቃ
ከትንሣኤህ ምኞት፣ ድንገት ስትነቃ
መንጋው ተሰልፏል፣ መጋዙን አሹሎ
ገዝግዞ ሊጥልህ፣ ከሥርህ መንግሎ።

ማክሰኞ 4 ኤፕሪል 2017

ተቀምጨ አያለሁ

አያለሁ ቁጭ ብዬ፣
ያለምን የጣር ምጥ
መድልዎና ሀፍረት
ወገኔ ጠውልጎ፣
ደምንባ ሲተፋ
አምኖ በከወነው፣
መልሶ ሲገፋ።

እመለከታለሁ፣
የህይወትን አተላ
እናት በልጆቿ፣ ተንቋሻ ተጥላ
ከመገፋት ብዛት፣
ሂዳ ስትጠለል ሞትን እንደጥላ።

እመለከታለሁ፣
ባፉ እንስት አጥማጅ፣ ከዳተኛ አማላይ
ጥሎሽ ነው እያለ፣
ግማሽ ጎኑን ሲያለብስ፣ ኦሜጋልባ ሰቃይ።

አያለሁ ጦርነት
ቸነፈር አያለሁ
አያለሁ አፈና
ስማእታት አያለሁ
አያለሁ እስረኞች
የግፍ ማራገፊያ፣
ዘብ አልባ ወደቦች።

ሕይን ሁሉ ስቃይ፣ እያየሁ ቆጥራለሁ
ጆሮዬን አቁሜ፣ ከልብ አደምጣለሁ
ቃል ካፌ ሳይወጣ፣ ጭጭ እንዳልኩ ሄዳለሁ።
እውን እኔ አለሁ?
________________________
መነሻ፣”I Sit and Look Out” —Walt Whitman

እኔን ብፈልገው

እንደ እፉዬ ገላ ፣ ቢቀለኝ ገላዬ
እንደ ህዋ ኮከብ ፣ ቢርቀኝ ጥላዬ
እንደ ሙታን መንደር ፣ ጭር ቢል ጓዳዬ
መንፈሴን አስሼ
ምናቤን ዳስሼ
ትግስቴ ተሟጦ ፣ መቅኔዬ ፈሷ'ልቆ
አየሁት ተንጋሎ ፣ እኔ ከእኔ ርቆ
ከዘመን ገደል ዉስጥ ፣ ተከስክሶ ወድቆ ።

እንደበራህ ለከሰምከው

ድቅድቁን ጥቁር ጨለማ ሰንጥቃ
ዛሬም ብርሃኗን ትለግሣለች ጨረቃ...

የማለዳ ኮከብም፣
እንደሁሌው ደማቅ ብሩህ ናት
ቀድማ ስትታይ ከንጋት ...

ፀሐይም እንደወትሮዋ ማልዳ ብቅ ትላለች
ፅጌረዳም ከደጃፌ ዛሬም ፀድቃ ትፈካለች...

ሰማዩ ዛሬም ሰማያዊ ነው
ወፎችም ይዘምራሉ
በቀስተደመና ክንፎች ላይ
ቢራቢሮዎችም ይደንሳሉ ...

ሁሉ ነገር እንደቀድሞው
አሁንም አለ ተንሰራፍቶ፥
ወዳጄ አንተ ብቻ የለህም፥
ከዚች ምድር ዳብዛህ ጠፍቶ።

ስለዚህ እኔን ከፍቶኛል፥
በምድራለሜ ደስታ ዘብቶ፥
ፈገግታም ከራቀኝ ሰንብቶ፥
ባንተ ሞት ውስጤ አንብቶ።
_________
መነሻ፣"To a Dead Friend", Langston Hughes
መታሰቢያነቱ፣ ላገኘው ስናፍቅ ሞቱን ለተረዳሁት ለዶ/ር ብርሃኑ ለገሠ።

ረቡዕ 15 ማርች 2017

አንድ ሰው

በህልምሽ ከፍቶሽ ስታነቢ፣
በ'ዉኑ እምባሽን 'ሚያብስ
ሌሎች ጊዜሽን ሲሻሙ፣
እርሱ እድሜውን 'ሚሰጥሽ
በአደይ ዝንታለም መስክ፣
የደስታሽን ዘር 'ሚዘራ
ነፍሱ የማትለመልም፣
አዝመራሽ ፍሬ ሳያፈራ...
ፍቅሩ ቁንጥር ያይደለ
ከእልፍ አእላፍ የዘለለ
እመኚኝ አንድ ሰው አለ።


ካፅናፍ አፅናፍ ቢንቆረቆር፣
የለቅሶሽ ርዝመት 'ማይገደው
ይልቅ እንባሽን ሰብስቦ፣
በሙቅ ተንፋሹ 'ሚያደርቀው
በዘመን ማማ ላይ ሆኖ፣
ዘመንሽን በልቡ 'ሚነካ
ፅልመትሽን ወዲያ ፈንግሎ፣
ደመና ምናብሽን 'ሚያፈካ...
ፍቅሩ ቁንጥር ያይደለ
ከእልፍ አእላፍ የዘለለ
እመኚኝ አንድ ሰው አለ።

ከስኬትሽ ፌሽታ ማልዶ፣
ዘልቆ ሕልምሽን ያለመ
ከመከናወንሽ ቀድሞ ሄዶ፣
ዛሬ-ነገሽን የተለመ
በንፍገት የታፈገ አየር፣
በተስፋ ሉባንጃ 'ሚቀይር
ከከፈለው ዋጋ ቀድሞ፣
የፍቅርሽን በረከት 'ሚቆጥር...
ፍቅሩ ቁንጥር ያይደለ
ከእልፍ አእላፍ የዘለለ
እመኚኝ አንድ ሰው አለ።

እጆችሽ በቆፈን ቆርብተው፣
የሙቀት ጠኔ ሲያበግናቸው
እጆቹ መድሃኒት ሆነው፣
ህዋሶችሽን 'ሚያክማቸው
የድዌ ፉፉቴ ሲገርፍሽ፣
ፈውስና ሠላም 'ሚጣራ
የዶፉን ድቅድቅ ሰንጥቆ፣
ፈገግታን ከፊትሽ 'ሚያበራ...
ፍቅሩ ቁንጥር ያይደለ
ከእልፍ አእላፍ የዘለለ
እመኚኝ አንድ ሰው አለ።

መነሻ: "Invisible Kisses" by Lemn Sissay

ሐሙስ 9 ማርች 2017

ከወርቅነት ወዲያ

አእላፍ ነው ዝምታ፣
በገለባ ቃላት
ባንገት በላይ ቅርሻት
በሃሜት ሹል ምላስ፣ በባዶ ድንፋታ
ግርማዊ ጥልቀቱ፣ ከቶ 'ማይረታ።

*****

ዝምታ ዉበት ነው፣
የእውነት ስብሃቷ
የሀቅ ደም ግባቷ
ያለም ጆሮ ቢቆም፣
ኡኡ አለማለቷ።

*****

ሰላም ነው ዝምታ፣
ፍፁም ብፁዕ እረፍት
ሀሴት ነው ዝምታ፣
የምናበ-ሹለት መመዘኛ ልኬት
የሕይወት ቅራሪ ከቶ ያልበረዘው
የንዋይ ሆምጣጤ ወትሮ ያልመረዘው።

*****

እንባ ዝም ያለ ነው፣
የአዞ ካልሆነ
ፈገግታም ዘም ያለ፣
ካንጀት ከበቀለ
ፍቅር ዝም ያለ ነው፣
ሲሆን ምክንያት አልባ
ሞትም መጥቶ ሲወስድ፣
በዝምታ ጩሀት፣ቀጥሮ ሳያግባባ።

ረቡዕ 8 ማርች 2017

ፍረጃ ህላዌ

ተናፍቆ ተናፍቆ፣
ሌት በቀን ሲተካ
ሞት መጥቶ ሲሰየም፣
በሕይወት መሥመር ዱካ
ሟች ሟችን አክሞ፣
ሟች ሟችን ሲያድነው
ሟች ሟችን አስታሞ፣
ሟች ሟችን ሲቀብረው
በትዉልድ ሰንሰለት፣ሰው በሰው ሲቀጠል
ለችግኝ መለምለም፣ጋሻ ዛፍ ሲቃጠል
በትርትሯ መሳ ጠብቃ መሰፋቷ
ላልጨበጥነው አልፋ ኦሜጋ አልባነቷ።

ረቡዕ 22 ፌብሩዋሪ 2017

ተጓዥ

ከቶ ያልጠበበኝ፣ የጥበት ስፋቱ 
ቅንጣት ያልጋረደኝ፣ የፅልመት ፍካቱ 
ተጓዥ ነኝ መሪ አልባ
ያለየልኝ ልዉጣ ልግባ
መድረሻ ፍለጋ 'ምዳክር
በመንገድ አልባ ምድር።

ያቆዩት ሕልም

ምን ይሆን ዕጣፈንታው፣ ሕልምን በይደር ሲያቆዩት?
ፀሐይ እንዳሸው ቴምር፣ ይሟሽሻል ይደርቃል?
ወይስ እንደ መረቀዘ ቁስል፣ በመግል ጠበል ያጠምቃል?
እንደ ከረመ ሥጋ፣ ክርፋቱ ከሩቅ ይጣራል?
ወይስ እንደ ጣፋጭ ጭማቂ፣ የስኳር ኮረት ያበቅላል? 
 ምናልባት፣አንደ ከባድ ሸክም፣ ከላይ ወደታች ይጫናል? 
ወይስ ቀን ሞልቶ ሲፈስ፣ ተወጥሮ ይፈነዳል?
------
መነሻ: "Harlem", Langston Hughes

ጀግና

ለወገኑ ሟችም
ወገኑን ገዳይም
ባንድ ቁና ስፍር፣ ይባላሉ ጀግና 
ለሰው 'ሚታየው፣ እንደየቆመበት ይለያያልና።

ምኑን

ኡኡታ ካስመነጠረ 
ዝምታ ካስጠረጠረ
ዋቲው በተድላ ካልዋለ
ማቲው በረካ ካላደረ
የመጠላለፍ ፈንጣጣ 
ባ'ጋርነት ጠበል ልፍልፎ ካልወጣ 
የ'ንባ ተራራ ካልተናደ 
 የበደል መጋረጃ ካልተቀደደ 
መዥገሮች ከትከሻ ካልወረዱ 
ዳኞች በሀቅ ካልፈረዱ 
 ገበታው ካልቀረበ ያለስጋት 
ወጉ ካልተወጋ ያለፍርሃት
ምኑን አዲስ ቀን መጣ 
ምኑን አደይ ፈነዳ 
ምኑን አየን አበባ 
ምኑን መስከረም ጠባ!

ነገ

ከሃሴት ከረጢት 
ስሜት ተሰድሮ 
 ከምናብ ጋን ሙላት 
 ክዳን ተስፈንጥሮ
የሀቅን ወለላ ጨለጥናት ባንዳፍታ 
የኋሊት እያየን ነገን በትዝታ።

ጉዞ

ዝግ በል ከ'ርምጃህ 
ቆም በል ከጉዞህ 
ጠይቅ መድረሻህን 
ሞግት መነሻህን
መንጋው ሲያለከልክ፣ማጣፊያው ሲያጥር 
 ትርታህን አድምጥ፣ እምነትህን አንጥር።