ረቡዕ 31 ዲሴምበር 2014

ማወቅ

"ማወቅ ሙሉ ያደርጋል" አሉን አዋቂዎች
ከቅርብ እያደሩ ፣ ተሩቅ ለምላሚዎች
የዋህነታቸው ፣ አለ-ማወቃቸው
ባዶዉን ጎደሎ ፣ አርገው ማየታቸው።
ሆኖ ታያውቅ ፣ ማወቅ ምሉእነት
ምጥቀት ፣ ባስተሳሰብ ገናናነት
ካ'ቻ'ንጎል መመንጠቅ ፣ ባተያይ ፣ በጢነት።
የማወቅስ ወጉ
ግፋ ቢልም ጥጉ
ወንፊትና ቁና ፣ ካ'ቻላይ ሳይነጥቁ
አንጓሎ ማጣራት ፣ ማወቅን ታ'ለማወቁ።
ባውቃለሁ ሳይረ'ቁ ፣ ሳይመፃደቁ
ማወቅን ከምግባር ፣ ሳይዋሹ ማስታረቁ።

ሰኞ 15 ዲሴምበር 2014

ምናለበት

በሚለበልበን እንደ ቆላ ጠሀይ
በምድጃ ጫማ ከምንቆጥር ሰቃይ
እኚህ ቻይናዎች ምነው ቢጠድቁብን
ጠሀይን ሚያስንቅ ወንበር ቢያበጁልን።

ረቡዕ 10 ዲሴምበር 2014

እምቢታ

አቦ-ሰጥ ንፋስህ ሹክ ባለህ ቁጥር ፣ አብሬህ አልነፍስም
መነሻ-መድረሻው ላልታወቀ ጉዞህ ፣ እግሬን አላሟሽም

ማክሰኞ 9 ዲሴምበር 2014

መርቀኝ ላልከኝ ወዳጄ

ሸለቆው ሜዳ እንዲሆንልህ
የማይሰበር እምነት ይስጥህ
የአይቻልም ተራራውን ከቶ አትፍራው
በፅኑ እምነትህና ትግስትህ ቦርቡረው
ቢጠፋ ቢጠፋ
አንድ የተስፋ ጠጠር መፈልቀቅ አይከፋ።

በቀቢፀ-ተስፋ ሸለቆ ተዉጠህ ሳለህም
በአለት ጣሪያና ግድግዳ ተከበህ ሳለህም
ዉድ ወዳጄ አይንሳህ የእዉን ሕልም።
ጨረስኩ አሜን አትልም?
ለምርቃት እኮ ምርቃት የለዉም  :-)

ሰኞ 1 ዲሴምበር 2014

ላልራመድ - ላልበር

ልቤ ገስግስ ይለኛል
ናፍቀሃል አግኛት ይለኛል
ገስግሼ መጣበት ፣ ጉልበትማ ነበረኝ
ካለሽበት ደርስበት ፣ ፅናትማ ነበረኝ
ብቻ አንድ ነገር ፣ አይቸግሩ ቸገረኝ...

ላብሮነታችን መሳካት ፣ የተስፋ ስንቄን ቋጥሬ
በቃልኪዳናችን መቀነት ፣ ቀጭን ወገቤን አስሬ
እግሬን ባቅጣጫሽ ቃኝቼ ፣ ለመራመድ ሲዳዳኝ
ሰርክ ወዳዘዝኩት ስፍራ ፣ ሳያቅማማ 'ሚወስደኝ
ልቤ መምጣትን ቢሻም ፣ እግሬ ላይሄድ ሞገተኝ...

የሚወደን ፣ የምንወደው
ያ ደጋጉ ፣ ያገር ሰው
"ጉድ ሳይሰማ..." ፣ አይደል 'ሚለው?
እውነት እኮ ፣ እዉነት አለው
ጆሮ አይሰማው የለ ፣ ስሚው...

ትዝ ይልሻል ያ መስካችን?
የነፃነት አየር መማጊያችን
በሰማያዊ ጣሪያ ተከልሎ ፣ ባረንጓዴ ምንጣፍ የተዋበው
ቀኑን በፀሐይ ዉጋጋን ፣ ሌቱን በጨረቃ ብርሃን 'ሚደምቀው
የት ጀምሮ የት ይለቅ ፣ ለ'ኛ ጉዳይ ያልነበረው
የባለ-ርስቱ ማንነት ፣ ድንበሩ ደንታ 'ማይሰጠን
ትንፋሻችን እስኪሟጠጥ ፣ ሳይታክት 'ሚያስቦርቀን...

ትዝ ይልሻል ሰበብ-አልባ ፍቅራችን?
ያልጠለሸው ልቦናችን ፣ ያልተበረዘው መንፈሳችን
በከዋክብት ጭብጨባ ታጅበን ፣ ነፍሴ ከነፍስሽ ስትዋሃድ
በፍቅር መንኩራኩር ተሳፍረን ፣ ከጠፈር ጠፈር ስንነጉድ
ብንካፈል - ብናካፍል ፣ ፍቅርና ፍቅርን ብቻ
ብንዘራ - ብንሰበስብ ፣ ፍቅርና ፍቅርን ብቻ
አይን ፣ ጆሮ ፣ ልብ የሌለን ፣ ለክፋትና ለጥላቻ...

አሁን ትዝ አለሽ ያ መስካችን?
የነፃነት አየር መማጊያችን...

እናልሽ፣ ቅድም ስነግርሽ
እግሬ ሞገተኝ ነበር ያልኩሽ?
ያለ ምክንያት እንዳይመስልሽ
ዝርዝሩ ከቶም አይረባሽ
ፍሬ-ነገሩን ብቻ ላውጋሽ...

ለመንገዱ ቁብ ሳልሰጥ፣ የመድረስ ጉጉት ስያቋምጠኝ
እግሬ እውነት ነበረው ፣ ላይራመድ ቢያብልብኝ
ያቅጣጫዬ ቅኝቱ ፣ ለእግሬ ምቱ ጠፍቶበታል
የነበረው በሙሉ ፣ እንዳልነበር ሆኖበታል
ያ ዉቡ መስካችን ፣ በ'ርቃን አለት ተተክቷል
ያ ደጋጉ ያገር ሰው ፣ ልቦናው ክፉኛ ደንድኗል
መስኩ ባየው ሆድ ብሶት ፣ እግሬ አውጣኝ ሸምጧል
ጨርቅ ማቁን ሳይሸክፍ ፣ አገር ጥሎ ኩብልሏል
መላወሻ የሌለው ፣ ዙሪያ ገባው ገደል ሆኗል።

ጉልበቴን ከፅናቴ ፣ በተስፋ ዉል አጣምሬ
መራመድ የተሳነኝ ፣ መቆሚያ አጥቶ እግሬ
ለምን አንደሆነ ፣ አሁን ገባሽ ፍቅሬ?

አንቺ'ኮ ንፁህ ተስፈኛ ነሽ
ደግ ደጉ ብቻ 'ሚታይሽ
መራመድ ከተሳነህ ፣ በርረህ ና የምትይው
ዉዴ ሌላ ፈተና አለ ፣ በጭራሽ ያላየሽው
ካማልእክት ብዋስም ፣ ክንፍ ለመብረርያ
እንዴት ልመንጠቀው ፣ ያለ መንደርደርያ?!

ረቡዕ 26 ኖቬምበር 2014

ተመኘሁ

ታልቀረ መመኘት
ተመኘሁ ዛፍነት
ከላዬ አራግፌ ፣ ጥውልግ ቅጠሎቼን
ቅርንጫፎቼ አድገው ፣ አጠንክሬው ግንዴን
እንዳዲስ ፀድቄ ፣ ለምልሜ ዳግመኛ
ለቅዥቴ ሳይሆን ፣ ለህልሜ እንድተኛ።

ቅዳሜ 22 ኖቬምበር 2014

አውቃለሁ

እርግጥ ነው በድዬሻለሁ
እውነት ነው ጎድቼሻለሁ
ሁሉንም ጠንቅቄ አውቃለሁ።

በናፍቆት ሰቀቀን
በመገፋት ቆፈን
እንደማለዳ ዉርጭ እንሰፍስፌሻለሁ።
አውቃለሁ።

ዱካዬን አጥፍቼ በፈለግሽኝ ጊዜ
ሰው አልባ አድርጌሽ በወንዝሽ በወንዜ
እንደቆላ ሃሩር አጠውልጌሻለሁ።
ይህንንም አውቃለሁ።

ሆኘ ያልሁንሁትን
ኖሮኝ የሌለኝን
በቁሜ ስቃዥ በቀን
ክፉ ህልምሽ ሆኘ እንቅልፍሽን ነጥቄሻለሁ።
ይህንንም አውቃለሁ።

ዳብሼ ሌላ ገላ
ጎርሼ ሌላ ከንፈር
በቅናት ማዕበል አናውጬ አዳፍቼሻለሁ
ከሰው ተራ አሽቀንጥሬ ወርዉሬሻለሁ
ከመሃል ጎተቼ ወደ ዳር ገፍቼሻለሁ
ከንፈርሽን በጥርሶችሽ አስነከሼሻለሁ።
ይህንንም አውቃለሁ።

እቶን ወላፈኑ ከሩቅ በሚንቦገቦገው
በበደል ምጣድ ላይ አገላብጨሻለሁ
አሻሮ እስኪወጣሽ እስክታሪ አምሼሻለሁ
ይህንንም አውቃለሁ።

እርግጥ ነው በድዬሻለሁ
እውነት ነው ጎድቼሻለሁ
ሁሉንም ጠንቅቄ አውቃለሁ።

ዉስጥሽ ግን እንዲህ ሲል ሰማለሁ...

ከበደል ከስቃይ ከበቀል ባሻገር
እጅ ባፍ 'ሚያስጭን የረቀቀ ምሥጢር
በልብ የሚዳሰስ ከስሜት ጥላ ስር
ምህረት አይገደዉም እውነተኛ ፍቅር።

ሰኞ 17 ኖቬምበር 2014

ያልታደሉት አጤ

እጅ አልሰጥም ብለው ትኩስ እሳት የጨለጡ
አጤው ጉድ አላዩ በልጆቻቸው እንደተበለጡ 
እጅ ከእግር ሰጥተው በራድ ዉሃ እንደሚጠጡ።

ረቡዕ 12 ኖቬምበር 2014

ባመድ አፋሹ እጅሽ

ያኔ፣
የጎረሱትን አላምጠው ፣ አጣጥመው ሳይዉጡ
ያጎረሳቸዉን እጅሽን ፣ መልሰው ሊንከሱ ሲሮጡ
ፊትሽ በምሬት ከስሎ ፣ ገር እንጀትሽ እያረረ
ሀቀኛው እንደበትሽ ፣ ተከፍቶ እያማረረ
"እጄ አመድ አፋሽ ነው" ብለሽ ነግረሽን ነበረ።

ዛሬ፣
ባንቺው ቅጥ-አጥ ቅጥፈት ፣ ጅስሚያችንን ካበገንሽው
የመንደዳችንን ነበልባል ፣ ለቆፈንሽ ማክሰሚያ ከሞቅሽው
አደራ ንፋስ ሳይቀድምሽ ፣ አመዳችንንም እፈሽው

ሐሙስ 6 ኖቬምበር 2014

ተከልሎ ላይከለል

በሕመማችን ልክ ፣ ደዌዉን ለሚያፀዳ
በጥማታችን መጠን ፣ ወይን ጠጁን ለሚቀዳ
በጠኔያችን ስፍር ፣ ለሚቆርጥ ፍሪዳ
ላዛኝ ቅቤ አንጉዋቹ ፣ ለባዕድ እንግዳ
ገመና ሊከለል ፣ መንገዱ ቢፀዳ
ዛፉ ሳር ቅጠሉ ፣ ቢመስል ፀአዳ  
ያ'ፍታ እድፍ እንጂ ፣ ችግር ላይፀዳ
...
ፍስሃን ደስኩሮ ፣ እንደሄደ እንግዳው
በተማፅኖ ትእይንት ፣ ይደምቃል ጎዳናው
ባ'ዳፋ ደግ እጆች
ባ'ሳዛኝ ዉብ አይኖች
በ'ውነተኛዎቹ ፣ የህላዌ መልኮች
በመሰንበት ትግል ፣ ሕያ ምስክሮች።

ሰኞ 3 ኖቬምበር 2014

ዘመኑን ለገደለ

በስንፍና ጠብ-መንጃው ፣ አቀባብሎ እያለመ
ምትክ-አልባ ዘመኑን ፣ አከታትሎ ላጋደመ
ጅብዱዉን ቆሞ ቢተርክ ፣ <<ካለ'ኔ ጀግና>> እያለ
ቁልቁል በሚያየው ግዳይ ዉስጥ ፣ እልፍ የራሱ ሞት አለ።

ሰኞ 27 ኦክቶበር 2014

የሁለት እስረኞች አጭር ወግ

ባይኑ ቀለም ሰበብ
የታሰረ ጓዴን ልጎበኘው ሄጄ
"እስር ቤት እንዴት ነው?" ስለው ለወዳጄ
እንዲህ አለኝ ልጄ ...

" እስር ምንም አይል
ነፃነትን ገፎ ነፃነት ያለብሳል
ትንሽ አስረስቶ ትልቁን ያስመኛል።
ይልቅ ልጠይቅህ...
ትልቁ እስር ቤት በቃ ተመቻችሁ?
በ'ዛ ክፍት ጣሪያው
ፀሐይ እና ዶፉን ሲያዘንብባችሁ
ሲሳይ መሰላችሁ? "

ረቡዕ 22 ኦክቶበር 2014

ግር

ልክ እንደ በግ መንጋ
ግር ብለው መጥተው
መስኩን ግጠው ግጠው
አፈሩን ለንፋስ
አለቱን ለፀሐይ
አሳልፈው ሰጥተው
በመጡበት ብሂል
ግር ብለው ሊሄዱ
ድንገት ሲሰናዱ
ግር ይላል መንገዱ።

ማክሰኞ 21 ኦክቶበር 2014

ጥፋት

ትናንትናችንን - ካጋባስንበት የታሪክ ረብጣ
ዛሬያችንን - ከቸረቸርነው ለእለት ቂጣ
ነገአችንን - ከተበደርነው ባ'ራጣ
ለ'ኛ ካለ'ኛ - ማን አለን አጥፊ ባላንጣ።

ሐሙስ 16 ኦክቶበር 2014

ተስፋ

እንደ ወፍ ነው ተስፋ፣ ክንፎቹ አማላይ
በርሮ ፣ በርሮ ፣ 'ሚያርፍ፣
ከነፍስ ቅርንጫፍ ላይ።

ተስፋ ባለ ጥበብ ፣ ተስፋ ባለ ክራር
በረቂቅ ጣቶቹ፣
ነገን በዉብ ዜማ ፣ ቃኝቶ 'ሚደረድር።

ምን ነካው?

አፈሩ ምን ነካው?
አየሩ ምን ነካው?
ምን አገኘው ዉሃው?
በላመ ማሳ ላይ
ምርጥ ዘር ስንዘራ
ባ'ረም የተሞላ
እሾህ የሚያፈራ?

ሰኞ 29 ሴፕቴምበር 2014

ዋርካው

ፅልመትን ሸኝተን ፣ ብርሃን ልናበስር
ተኮልኩለን ነበር ፣ ከትልቅ ዋርካ ስር
ከፍታን ለማየት ፣ ሲቃና አንገታችን
በዋርካው ቅጠሎች ፣ ተጋረደ አይናችን
ከዋርካው በስተላይ፣ ከጥላው ባሻገር
አድማስ ይንጣ ይጥቆር ፣ አልገባንም ነበር።
ባ'ንድ በገዳም ቀን
ባ'ንድ ክንድ አብረን
ያንን ግዙፍ ጥላ ፣ ያንን ግዙፍ ዋርካ
ገዝግዘን…
ገዝግዘን…
ከስር መሰረቱ ፣ ነቅለን ስናበቃ
ፀሐይ አሸልባ ፣ ነቅታለች ጨረቃ።

ሐሙስ 25 ሴፕቴምበር 2014

ማንም - ከየትም

 'ማልመደብ ከክርስቲያኑ ፣ ከሙስሊሙ ወይ ካ'ይሁዱ
'ማልፈረጅ ከቡድሃው ፣ ከሱፊው ፣ ከዜኑ ወይ ከሂንዱ
ከሃይማኖት ወይ ከባህል 'ማይመራኝ መንገዱ
ያልመጣሁ ከምሥራቁ ወይ ከምዕራቡ
ያ'ይደለሁ ከሰሜኑ ወይ ከደቡቡ
ያልፈለቅሁ ከባህሩ ፣ ከጥልቁ ከውቅያኖሱ
ያልወረድሁ ከደመናው ፣ ከሰማያዊ ክርታሱ
ከትቦ ያላስቀመጠኝ ፣ የፍጥረት ሀተታ ድርሳን
ዘሬ ግንዱ 'ማይመዘዝ ፣ ካ'ዳም እና ከሔዋን
ስፍራዬ ስፍራ የሌለዉ ሊጎበኘኝ ለሚተጋ
ዱካዬ ዱካው 'ማይገኝ የሚፈትን ለፍለጋ
መደብ ያልተበጀልኝ ከመንፈስ ወይ ከሥጋ
አይደለሁኝ ማንም
አይደለሁም የማንም
ከዚህኛዉ የለሁም
አልኖር ከሚመጣዉም
ያልመጣሁኝ ከየትም
የማልሄድ ወደ የትም
ማንም ነኝ ከየትም።

***********************
የ "Rumi"ን "Only Breath" የተሰኘዉን ግጥም አንብቤ ሳበቃ በ'ኔው ገልቱ ትርጉም ወደ አማርኛ የተቀየረ

ሐሙስ 18 ሴፕቴምበር 2014

ስካር

በላይ በላዩ ላይ ስትጨልጥ አምሽተህ
ከሚጠጣ ነገር ሽጉጥ ብቻ ቀርቶህ
ጎህ ሲቀድ ሰማይ በቀዝቃዛ ጠዋት
"የት ገባ ራስ ምታት?"
"የት ገባ ማዛጋት?"
እያልክ አትሸበር
በፍቅር ሲሰከር
የለዉም ሀንጎቨር።

ረቡዕ 17 ሴፕቴምበር 2014

ምልከታ

ያዘቦት ቀን፣
                   ቁራጭ ሕይወት
መንቃት፣
                   ሽራፊ ዉልደት
ብሩህ ማለዳ፣
                   ጉማጅ ወጣትነት
እንቅልፍ፣
                   ስባሪ ሞት።

ሰኞ 15 ሴፕቴምበር 2014

ስለ ሞገደኛው ፍቅርሽ

ላወጋሽ ስከጅል ፣ ታሪኬን ዘርዝሬ
በትዝታ ክንፌ ፣ የኋሊት በርሬ
ድው! ድው! እያለ ፣ እንደ ጠንቋይ ዲቤ
በጉግስ ትርታ ፣ እየመታ ልቤ
ከወዳደቀበት ፣ ትንፋሼን ሰብስቤ
የድፍረትን አየር ፣ በረ....ዥሙ ስቤ
በብርክ ማዕበል ዉስጥ እንደተሳከረ
ከወዲያ ከማዶ ይጣራ የነበረ
አስገምጋሚው ድምፄ ፣ ጭጭ ብሎ ቀረ።

ሻል ያለኝ ሲመስለኝ
እንዲህም አስመኘኝ

ቃላት ከፊደላት ሰብስቤ
ሃሳብ ባ'ሳብ ላይ ደርቤ
አንደበቴ ተሞርዶ እንዳለቀ
ሃሳቤ ባ'ንዳፍታ ተፍረከረከ
ድንጋይ አንደመታው መስታወት ተሰነጠቀ።

በማዕበላማው የፍቅር ባህርሽ
ጀልባዬ ብትሰጥም አይግረምሽ
እንኳንስ የ'ኔ ኢምንት ጀልባ
ካንቺ ዉብ አይን ከቶ 'ማትገባ
ተወርዋሪው የፍቅርሽ ማዕበል
ግዙፉን መርከብም ያሰጥማል።

የፍቅርሽ ወጀብ ብርታቱ
ተተርኮ ላይዘለቅ ጥልቀቱ
ኮስማና ጀልባዬን አንስቶ
ካ'ለት ከቋጥኙ አጋጭቶ
ያረጀ አካላቷን ፈታትቶ
መደገፊያ ዘንጌን ነስቶ
አንደ'ዜ በፍቅርሽ ማዕበል ስደገፍ
ሌላ'ዜ በወጀቡ ተገፍቼ ስንሳፈፍ
ለይቼ ሳላውቅ ኩነቴን
መኖሬን ወይ አለመኖሬን
መሆኔን ቆሜ ሳበስር
አለመሆኔ ሲነቅለኝ ከሥር
በመኖሬ መኖር ሳጓራ
አለመኖሬ ገዝፎ ከጋራ
ወዲህ ረከስኩ ብዬ ስቆዝም
ወዲያ ዋጋዬ ንሮ ስደመም
ስሞት ስነሳ በፍቅር
ስለ ትንሣኤ መኖር
ከቶ እንዴት ብዬ ልጠራጠር?

ማክሰኞ 2 ሴፕቴምበር 2014

ዉዴ

አንቺን የሚመጥን ስጦታ ፍለጋ፣
ቁልቁለቱን ወረድሁ
አቀበቱን ወጣሁ

ወርቅ እንዳላመጣ፣
ከ'ግር እስከራስሽ እንድታጌጪበት
ካንቺ ወዲያ ላሳር ፣ በወርቅ አንጣሪነት

ጠጅ እንዳላመጣ
በአልማዝ ብርሌ ፣ ተቀድቶ 'ሚጠጣ
ካንቺ ወዲያ ጠጅ ጣይ
እንኩዋንስ ዘንድሮ ፣ ለርከርሞም አይታይ

ልቤን አንዳልሰጥሽ
የኔን ልብ የገራ ፣ አውራ ልብ የታደልሽ
ከሥጋ ነጥዬ ፣ ንፍሴን እንዳልቸርሽ
የኔ ብኩኗ ነፍስ ፣ ላንቺ 'ማትመጥንሽ

ያየሁት በሙሉ ካ'ይን 'ማይገባ ፣ የልብ 'ማያደርስ
ሆኖብኝ ልፋቴ ፣ ዉቅያኖስ በሲኒ ቀድቶ እንደመጨረስ
ቢጨንቀኝ ቢጠበኝ ፣ መስታወት ሰጠሁሽ
ራስሽን ስታዪ ፣ ድንገት ትዝ ብልሽ።

ረቡዕ 27 ኦገስት 2014

እጅ የሰጠን

ከቶ አትጠየቅ "ለምን?" ትብለህ
ምን አሳቀቀህ ፣ ማን ሊሞግትህ
እንዳሻህ ጠርቅ ፣ ተርትር ነገርህን
የ "አሉ" ቱባ ፣ የወሬ ክምርህን
ሎጋ ምላስህን ፣ ሳለውና
በሾለው በኩል ፣ ሞርደውና
ቁረጥ ፣ ዘልዝል ፣ የወሬ ሻኛ
"ታመመ" ሲሉህ ፣ "ሞተ" በል ለእኛ
እኛ እንደሆንን፣
"ለምን?" ፣ "እንዴት?" 'ማይገደን
በ "መሰለኝ" ባህር የተወዘትን
የምይሞቀን ፣ የማይበርደን
ለምላስ ጀግና እጅ የሰጠን
ኩሩ የ "አሉ" ምርኮኞች ነን።

ማክሰኞ 5 ኦገስት 2014

መሃረቤን

"መሃረቤን ያያችሁ"
ብዬ ሳጫውታችሁ
"አላየንም" ላላችሁ
ሄድኩኝ እዛው ትቻችሁ።

መሃረብ ልሸምት ወጣሁ
ገበያዉን አዳረስሁ
ብዞር ከጫፍ እስከ ጫፍ
ተወዷል መሃረብ እንደ ጤፍ።

"ለምን?" ብዬ ብጠይቅ
ይመልሳል ባለሱቅ
መሀረብ የተወደደው
ዋጋው ሰማይ የነካው
ብልፅግና ኮርኩሮት፣
እንባው "አልቆምም!" ያለው
በሳቅ የሚያነባ፣
ሸማች ስለበዛ ነው።

ማክሰኞ 22 ጁላይ 2014

መራራቅ

ከ'ልፍ ማይሎች ልኬት ፣ ካድማስ የዘለለ  
ሰርክ ባንድነት ሆኖ እንዳ'ለመግባባት፣
 ምን መራራቅ አለ።

ሰኞ 14 ጁላይ 2014

በዚህ በጉድ አገር

በዚህ በጉድ አገር፣
መንገድ ላይ ማላመጥ ፣ ነውር በሆነበት
አደባባይ ቆሞ፣
እችግኝ ላይ መሽናት ፣ ማን ከልካይ አለበት።

በዚህ በጉድ አገር፣
በያደባባዩ፣
ባይነ-ህሊና ድሪያ ፣ ደም-ሥር ሲውጠረጠር
ስለወሲብ ማውጋት፣
በሹል ቃል አሳዶ ፣ ያስወጋል በነገር።

በዚህ በጉድ አገር፣
አንጀት ከድቶት ዝሎ ፣ ያገር ልጅ ሲያቃስት
ባርምሞ ምልከታ፣
ከንፈር መምጠጥ እንጂ ፣ ማን ከመጤፍ ቆጥሮት።

በዚህ በጉድ አገር፣
ጉልበተኛ ሲነጥቅ ፣ ላብ-አደር አፍኖ
መንገደኛው ያልፋል፣
በምን-ገዶኝ ግርዶሽ ፣ ማያዉን ሸፍኖ።

በዚህ በጉድ አገር፣
ጥራዝ-ነጠቅ ስያኝክ ፣ የቅልለትን ቅጠል
ትውልድ አሰልፎ፣
ያጠምቃል ሊህቁ ፣ የፍርሃትን ጠበል።

ዓርብ 11 ጁላይ 2014

ዋ!

ላ'የር ላይ መንበርሽ
ለዛፍ ላይ መኝታሽ
ዝናሩ የዲናር ፣ ጋሻው የብረት
ቋጥኝና አሸዋ በቋፍ ለያዙት
ዋ! ወዮሁለቱ
ዋ! ሰጋሁለቱ
የከሰለው ፍሞ፣
የከሰመው ግሞ፣
የተነሳ እንደሆን ፣ የሰደድ እሳቱ!

ፍቱን

የእውነት ዝናር ታጥቃ
የተስፋ ጦር ሰብቃ
ትእቢቷን አዉልቃ
ካንድ ራሷ ታርቃ
ተነስተው ፣ ተራጋጭ እግሮቿ፣
ተፈትተው ፣ ታሳሪ እግሮቼ፣
ያ'ፍ ልጓሜ ቢል-ላላ
እመሃል መንገድ ላይ፣
የሚታይ ለሚያይ፣
ቁብ ሰጥቶ ለሰማ፣
ዋይታው የሚሰማ፣
ለእርሷም የሚበጃት ፣ ለእኔም ያላደላ
ነፃነት የሚባል ፣ ነበር ፍቱን መላ።

ማክሰኞ 1 ጁላይ 2014

ተማፅኖ ወጎዳና

ለእናንተ ጎዳና ፣ ሰርክ መመላለሻ
ለእኔ ጎጆዬ ነው ፣ መረሳትን መርሻ
ለእናንተ መቆሚያ ፣ ወይ መተላለፊያ
ለእኔ ኑሮዬ ነው ፣ መገፋትን መግፊያ።

ላስመሳዩ ጓዴ

ለጥ ባለው ሜዳ ፣ ረግረግ ባልዞረበት፤
ከፊቴ እየቀደምክ ፣ መንገድ እንዳልመራክ፤
ድጥ እና ማጥ መሃል ፣ ሲገላበጥ ጎኔ፤
እንኳንስ ከፊቴ ፣ የለህም ከጎኔ።

ዓርብ 6 ጁን 2014

ቢቸግረኝ

በሰው መንጋ ተከብቤ
እውነት ሲሆን ጥሜ ራቤ
የሀቅ ልሳን ግቷ ነጥፎ
ክህደት ሲያዳፋኝ ጠልፎ
በቅጥፈት ጥላሸት ተለቅልቄ፣
በብቸኝነት ስለከሰልኩ
ዋሾ ወዳጄን ሸኝቼ፣
ታማኝ ባላንጣዬን ተቀበልኩ።

ሐሙስ 5 ጁን 2014

የበላኝ ጅብ

ሳያማትር ዙርያ ገባውን፤
ሳያደምጥ የገዛ ጆሮዉን፤
ባንክሮ አቀርቅሮ ከዘንጠለ፤
ሲጠሩት "አቤት" ካላለ፤
ድምፅ ፣ ትንፋሹን አምቆ፤
ጥላ ፣ ኮቴዉን ደብቆ፤
የበላኝ ጅብ ፀጥ ካለ፤
ከሁለት አንድ ነገር አለ...
ወዲህም ላይጠራ ቢጤዉን፤
ወዲያም ባይሞላ ስልቻውን።

ሐሙስ 29 ሜይ 2014

ምፀት

በጠራራ ሌሊት ፣ በብሩህ ጨለማ
ይሞቀኛል ገላሽ ፣ አልደርብም ሸማ 
ይታየኛል ፊትሽ ፣ አልለኩስም ሻማ።

ብራና

ጥበብህ ተዳፍኖ ፣ እንዳትቀር መና፤
ፅልመቴ ተገፎ ፣ ዉልግዴ እንዲቃና፤
ከጋንህ ተላቀህ ፣ አሳየኝ ብራና።

እሑድ 25 ሜይ 2014

ትከሻ

አፈርማ አይደለም ፣ እምራመድበት፤
በድን መሬት አይደል ፣ በእግሬ የረገጥሁት፤
ባማተርሁኝ ቁጥር፣ በተንጠራራሁኝ፤
ከፍ አርጎ አያሳየ ፣ ነገዬን ያስቃኘኝ፤
ቁሞ የተሸከመኝ ፣ ወድቆም የደገፈኝ፤
የእልፎች ትከሻ ነው ፣ አፅንቶ ያቆመኝ።

ሐሙስ 22 ሜይ 2014

ተጓዥ

ቀኑን ፣ ስጓዝ፤
ዉዬ ፣ ስጋዝ፤
ምሽቱን ፣ ተቀብዬ፤
ካረንጓዴው ፣ ማሳዬ፤
በጀርባዬ ፣ ተንጋልዬ፤
አኝጋጥጬ ፣ ከሰማዬ፤
ባብረቅራቂ ክዋክብት ታጅበን፤
እኔ እና እኔ ፣ ጭልጥ ብለን ጠፍተን፤
አቅጣጫ አልባ ፣ ተጓዥ ሁነን፤

በፍጥነት እየከነፈ...............

ደራሽ ፍርሃት ፣ ልቤን ገምሶት አለፈ፤
የረሳሁት አገረሸ ፣ ያላየሁት አሰፈሰፈ፤
እረፍት አልባው እኔነቴ፣
ሰዉ-ነቱ ተንዘፈዘፈ።

እኔ ወደ እኔ ዘንበል ስል..........

የመጣሁበትን ፣ ሳብሰለስል፤
ያልሄድሁበትን ፣ ባይነ-ህሊናዬ ስስል፤
የማላውቅ ፣ ልዉጣ ልግባ፤
ሆንሁኝ ተጓዥ ፣ መሪ አልባ፤
መድረሻ ፍለጋ እምዳክር፤
በመንገድ አልባ ምድር።    

ማክሰኞ 20 ሜይ 2014

አመድና ዱቄት

በንፋስ ታንኳ ላይ ፣ አብረው ሽው እያሉ
አመድና ዱቄት ፣ በሳቅ ይፈርሳሉ።

ሰኞ 19 ሜይ 2014

ህልሜ

ራሷን በራሷ ነክሳ፣
           ደመ-ከልብ ከሚሆን ደሟ
አጥንቷን ባጥንቷ ሰብራ፣
           ከምትደፋ ባፍጢሟ
ባብራኳ ክፋይ ሟች-ገዳይ፣
           ዞትር ደረቷን ከምትደቃ
ማየት ነው ህልሜ ተስፋዬ ፣
          እናቴ ከእናቷ ታርቃ።      

ዓርብ 16 ሜይ 2014

የቸገረ ነገር

ያብሮነት ሲሆን መዝሙሩ፤
ክርሮ ከተወጠረ ደም-ሥሩ፤
የብርሃን ጎዳና ስትጠቁመው፤
የፅልመት ጉራንጉር ከዋጠው፤
አይኑ እያየ የሰው ምስል፤
ልቡ ክፉ አዉሬ ሲስል፤
ባንድነት አልጋ ተተኝቶ፣
በልዩነት ደወል ከተነቃ፤
ዛሬን ማለፍ ዳገት ሆኖ፣
ነገም ዘበት ሆነ በቃ።

ሐሙስ 8 ሜይ 2014

አንቺን ያገኘሁ 'ለት

አንቺን ያገኘሁ 'ለት፥

ቁሩን አንዳልሸኘች፣
               ምድሪቱን አሙቃ፤
ፀሐይ ያላመሏ፣
               ዋለች ተደብቃ፤
ካንቺ ትንፋሽ በላይ፣
               እንደማትሞቅ አውቃ።

አንቺን ያገኘሁ 'ለት፥

የሊቅ የደቂቁን፣
               ቀልብ አንዳልሰለበች፤
ሽሙንሙን ጨረቃ፣
               ደመና ለበሰች፤
ካንቺ ዉበት ልቃ፣
               ልቤ ስላልገባች።

አንቺን ያገኘሁ 'ለት፥

ዞትር በምሽቱ፣
               አይኔን 'ሚያዋልሉ፤
"ከኛ ወዲያ አድማቂ ተገኘች"፣
               እያሉ፤
ክዋክብት ለክብርሽ፣
               ከሰማይ ዘለሉ።

ማክሰኞ 6 ሜይ 2014

እስራት

አይደለም መቀፍደድ፣
               በብረት ሰንሰለት፤
አይደለም መከርቸም፣
               በዝግ ጨለማ ቤት፤
አይደለም መወርወር፣
               ከምድር በታች ግዞት፤
አይደለም መነጠል፣
               ከሰው መንጋ ምቾት፤
የመጠፈር ወጉ፣
የመሸበብ ልኩ፣
የመታሰር ጥጉ፤
በህሊና ወህኒ፣
              መንፈስ መጠፍነጉ።
በህሊና ችሎት፣
             ፍትህ መጠውለጉ።

ሰኞ 5 ሜይ 2014

መስለን

እንዳልከተልሽ፥
ጀርባሽ ፣ ጎራንጉሩ፤
እንዳላስከትልሽ፥
ጀርባዬ ፣ ሰንበሩ፤
የቁርጥ ቀን መጥቶ ፣ እስኪያፋጥጠን፤
እናዝግመው እንጂ ፣ ሁነን ጎን-ለ-ጎን፤
ለተከታያችን ፣ መስለን የተማመን።

ልትለኝ ፈልገህ...

በዚያች ዕለተ - ብሽቅ፥
በዚያች ጠዋተ - እንቅ፥
ባዲስ ተስፋ ጮራ፣
                   አይኖቼ የፈኩ፤
ያንተም ያለወትሯቸው፣
                   የተገረበቡ፤
በዝጉ አንደበትህ፣
                   ተረግዞ ነው መልእክት?
ለማዋለድ ነበር?፣
                   ያይኖችህ መዋተት
ምነው ባገር ሰላም?፣
                   ጠግበህ ማታገሳ
ትንፋሽ ራቀህ'ሳ፤
                  ተርበተበትህ'ሳ?
በቃህ ተንበረከክህ?
እጆችን ሰጠህ?
ጭራሽ ተመቻቸህ?
ክንድህ ትራስ ሆነህ?
*     *      *      * 
በዚያች ዕለተ - ብሽቅ፥
በዚያች ጠዋተ - እንቅ፥
ትዉስ ባለኝ ቁጥር፣
                  ያይኖችህ ዋተታ፤
                  የጆችህ ቧጠጣ፤
"በነበረው..." እላለሁ፣
ቅራፊ እስትንፋስ፣
                  ሽራፊ ደቂቃ፤
ምላስ ለማላቀቅ፣
                  ከደረቀ ላንቃ።


*     *      *      * 
ትዉስ ባለኝ ቁጥር፣
                  ሰርክ ይወጋጋኛል፤
                  ይሸነቁጠኛል፤
ልትለኝ ፈልገህ፣
                  ላትለኝ የቻልከው፤
አይንህ እንደዋተተ፣
እጅህ እንደቧጠጠ፣
ወዳይቀሬበት፣
                  ይዘህ የወረድከው።

ማክሰኞ 29 ኤፕሪል 2014

ሰሚ ማጣት

አንገቴ አይል ቀና ፣ እንዳምናው ዘንድሮ፤
በደም መጣጭ ተባይ ፣ ጫንቃዬ ተወሮ።
ከላዬ አሽቀንጥሬ ፣ አላፈርጠው ነገር፤
እጄ ተጠፍሯል ፣ ግራው ከቀኙ ጋር።
እንዳልደባልቀው ፣ መንደሩን በሩምታ፤
ልጉሙ ልሳኔ ፣ ነጥፏል ለኡኡታ።
የጆሮ ኩሊ እንጂ ፣ ሰሚ በሌለበት፤
በግፍ አዳራሽ ዉስጥ ፣ ጥግ ይዤ በትዝብት፤
በዝምታዬ ፍም ፣ አቀልጣለሁ ጩኸት።

ዓርብ 25 ኤፕሪል 2014

ያገሬ ባላገር

"ቀለም የዘለቀኝ" - ብለህ ካልተኮፈስህ
ካፈር መደቡ ላይ - አብረህ ከተሰየምህ
የከተበልህን - እንቶኔ አሰማምሮ
የለቃቀምከውን  - ዙረህ እንደ ጭራሮ
ወረቀት ከብእር - የግድ ሳያዋድድ
ከህሊናው ማህደር  - ይቀዳዋል ለጉድ።

ትረካ በእጁ  -  ማዋዛት በደጁ
ምን ብዥታ ቢብስ - በንቅልፍ ቢያንጎላጁ
የኋሊት ለማየት - አይኖቹ አያረጁ።

"እኔ አውቅልህ" ብሎ - ባዕድ የጋተህን
"ወገኔ" ምትለው - ያወላገደውን
የታሪክ ጠቃሚው  - የደራረተውን
ቀንና ሰዓቱ - ሳይዛነፍ ውሉ
ሳይለቅ ቀለሙ - ሳይደበዝዝ ምስሉ
በትዝታ ፈረስ  - በዘመን ኮርቻ
አፈናጦ ሚያደርስ - ከኩነት ዳርቻ
ላገሬ ባላገር አጣሁለት አቻ።

ረቡዕ 23 ኤፕሪል 2014

ጎብጦ

እንዴት ቀና ልበል ፣ አንደምንስ ብዬ፤
በፋታ-አልባ ሸክም ፣ ጎብጦ ትከሻዬ።

ጠራቢ እጆች

በነኛ ዉብ እጆች ፣ በድንጋይ ጠረባ
ያክሱም-ላሊበላ ፣ ጥበብ ተገነባ።
የኚህን ድንቅ እጆች ፣ አሻራ መርምረው
ፀሐይ 'ማይከልል - ዝናብ 'ማያስጠልል፣ ቆባቸውን ደፍተው
በተርታ ተሰጥተው በየ-ምን-ገዱ ላይ
ዛሬ ቀንም እጆች ይጠርባሉ ድንጋይ።

በላቡ

የመንደራችን ሹም ፣ መኳኳሉ በዛ
ሁሉም አያወቀው ፣ በላቡ እንደወዛ።

ገበያው

ሸቀጡ ለጉድ ነው ፣ ገበያውም ደርቷል 
ዋጋው በማይጎዳ ፣ ባገር ሻጭ ተሞልል።

አትዙር!

ወደ ኃላ አትዙር! ወደፊት አተኩር!
ትይኝ የነበረው ፣ ናላዬ እስኪዞር፤
ያመጣንን መንገድ ፣ እንድረሳው ነበር?
ይብላኝ እንጂ ላንቺ፣ እኔስ አገኘሁት፤
ጥምዝምዙን መንገድ ፣ መልሼ አሰመርሁት፤
የጀርባሽ ነፀብራቅ ፣ በፈጠረው ጨረር፤
ወለል ብሎ ታየኝ ፣ እጥፋቱ ጭምር።

ሰኞ 21 ኤፕሪል 2014

ገዥና ሻጭ

የጥንቱ ነጋዴ ፣ ስንፍናው ላሳር ነው፤
መሸጥ አይችልበት ፣ መግዛት ካባቱ ነው።
የዘመኑ ጮሌ ፣ ብልጥ ነው ጨላጣ፤
መግዛቱ ሳያንሰው ፣ በንጣቂ ረብጣ፤
አንደ'ዜ በጥቅል ፣ ሌላ'ዜ ቆንጥሮ፤
ባ'ራጣ ይሸጣል ፣ ወለድ ተደራድሮ።

ዓርብ 18 ኤፕሪል 2014

ተነድፏል

አትደነቁ ቢያወራ፣
ቆሞ ከጥላው ጋራ፤
አይጭነቃችሁ ቢባንን፣
ከምትጣፍጥ ሰመመን፤
አይግረማችሁ ቢያውካካ፣
በዱር በገደል በጫካ፤
አትሳቀቁ በርቃኑ፣
ገላው ቢከዳው ሽፋኑ፤
አትሳለቁ ቢያደናቅፈው፣
የ'ውነት ገመድ ቢጠልፈው፤  
ከምንይሉኛል ተኳርፎ፣
ባይለቄ ልክፍት ተለክፏል።
በሀቅ ትንኝ ተነድፏል።

አባልቶ

በጠኔ ጠውልገን ፣ ባየን ጊዜ አዘነ 
አዝኖም አልቦዘነ ፣ ሊያጠግበን ወጠነ
እጃችንን ታጠብን ፣ እጆቹን ታጠበ
ከሞላው ገበታ ፣ ሊያባላን ቀረበ
ካጥንት ከመረቁ ፣ እያሳለፈልን 
ከጠላ ከጠጁ ፣ ሲያንቆረቁርልን 
እስክንሰክር ፣ አጣጥቶ
እስክንጠግብ ፣ አባልቶ
እርሱ አሸለበ፣ 
እኛን እንቅልፍ ነስቶ።

ማክሰኞ 15 ኤፕሪል 2014

አበረታኝ

ወፌ ቆመች ከማለቴ
ሲያርቋት ምርኩዜን ከፊቴ
ቀና ስል ላይ ከፍታ
በኩርኩም አናቴ ሲመታ  
ስጀምር መሄድ መራመድ
ሲያረጉት እግሬን ሽምድምድ
እንደለመዱት ሊያመክኑት
መንፈሴን ሲቀጠቅጡት
እንኳንስ ተሰብሮ ሊያሳጣኝ
ካለት ፀንቶ አበረታኝ።

እሑድ 13 ኤፕሪል 2014

አንቺ'ኮ

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
ሙሉ ጉባኤ ሲስቅልኝ
ፈገግታዬን ሲያፀድክልኝ፣    
ሰርስረሽና ጎርጉረሽ
ልቅም አርገሽ አበጥረሽ
አንግዋለሽና አንጥረሽ ፣
ከሚያስንቅ ግዙፍ ጋራ    
ከክምር ፈገግታዬ ተራ
ያዘኔን እሾህ ትመዣለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
ተሰፍቶ ጥርሴ ከከንፈር
ወይ አልናገር ወይ አልጋገር
"ጋግርታሙ!" ሲለኝ አገር፣
ሳልተነፍስ ሽራፊ ቃል
ጠጠር ከልሳኔ ሳልወረውር፣
ፀጥ ያለዉን ፀጥታዬን
ልቤ ላይ ጆሮሽን ደቅነሽ
የጥሞና አደማጬ ነሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
እሳት ለብሼ እሳት ጎርሼ
ሳስቸግር ለያዥ ለገራዥ፣
ደሜ ሞቆ ሲያተኩስ
ቀረርቶዬ ሞልቶ ሲፈስ፣  
ከንዴቴ ነበልባል ወስደሽ
የእሳት ደመና ሰርተሽ  
የፍቅር ዶፍ ታዘንቢያለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።
በስስት ሲቃ ሳቃስት
አይኔ ከማዶ ሲቃትት፣
ጨረቃን በምናቤ ሳቅፍ
ክዋክብት ከሰማይ ሳረግፍ፣
ስሜት ሲያረገኝ ወፈፍ
ከንፈሬ ከንፈርሽን አፈፍ፣
በሃሴት ቀልጬ ስከንፍ
በንዝረት ባህር ስንሳፈፍ፣      
ስትዳባብሽኝ ባይኖችሽ
የናፍቆትን ጉም በትነሽ
የርካታ ጠበል ትረጫለሽ።

አንቺ'ኮ እጡብ ድንቅ ነሽ፣
እውነት የእውነት ነሽ፣
ከልብሽ አይናማ'ኮ ነሽ።

ምነዋ ጣይቱ?

ፍጥረት አይኑን ገልጦ
ግራ ቀኙን ቃኝቶ
ተንጠራርቶ ተጠራርቶ፣
ምድር ፊቷን አፍክታ
ቆፈኗን በጮራ ተክታ፣
ምኞት ከተስፋ ሰንቆ
አንጀቱን ቋጥሮ አጥብቆ፣
ዱር ገደሉን ሊያቀና
ወገን ባለ ደፋ-ቀና፣
ባንቺ በጣይ'ቱ
በብርሃን ለጋሲ'ቱ፣
ስታሞቂን በፈገግን
ስታበስይን በሞከክን
እያረርንም እንደሳቅን
እያከሰልሽ አሳመድሽን።
ግን ለምን ጣይ'ቱ?!
ብርሃን ለጋሲ'ቱ!
አንፀባራቂ'ቱ!

ዓርብ 11 ኤፕሪል 2014

አዋራጄ

ወጥቼ አቀበቱን ፣ ያላንዳች እገዛ
ቁልቁል ስንደረደር ፣ አዋራጄ በዛ።

አስባ'ለሁ

ሃሳብ አወጣ'ለሁ፣
እሸከመዋ'ለሁ፣
ሃሳብ አወርዳ'ለሁ፣
ባሳብ እወጣ'ለሁ፣
እንጠላ-ጠላ'ለሁ፣
እወዛ-ወዛ'ለሁ፣
እንሸራተታ'ለሁ፣
ባሳብ እወርዳ'ለሁ፣
ሃሳብ አስባ'ለሁ።

ረቡዕ 9 ኤፕሪል 2014

ይመስገነው አለን

ይመስገነው አለን ፣
ቁጥርን እንደ ቁርጥ
ቆርጠን እየበላን፣

ይመስገነው አለን ፣
እምባን እንደ አምቦውሃ
ቀድተን እየጠጣን፣

ይመስገነው አለን ፣
ጨለማ እንደ ፋኖስ
ዞትር እያበራን፣

ይመስገነው አለን ፣
ቁጭት እንደ ባቡር
ተሳፍረን ሽው እያልን፣

ይመስገነው አለን ፣
እጅግ እንደረቅቀን
እንደተንደላቀቅን
እየሌለን አለን።

መጥዋቹ

አዛኝ የሚመስለው
ከንፈር የሚመጠው
የፀዳ የነጣ ኩታ የሚለብሰው
ለጥድቅ እጅ መንሻ እጁ የሚፈታው ፣
ይሄ እልፍ አሕዛብ ይሄ እልፍ አማኝ
የሚርመሰመሰው ባለፍኩ ባገደምኩኝ
ቤሳ ሲጥል እንጂ ሲሰጥ አላየሁኝ።

NB: Inspired by Bewketu Seyoum's "The road to nowhere" on Modern Poetry in Translation

ማክሰኞ 8 ኤፕሪል 2014

እ-ና-ሸ/ቸ-ን-ፋ-ለ-ን!

ያ ጓዴና እኔ፣ ፊትለፊት ተያየን
"ወዴት ነህ ? "ተባባልን
ኢላማ ግባችን እንድነቱን አወቅን።

ፅዋችንን ሞልተነው
ለድላችን ከፍ አርገነው
አጋጭተንም ቀመስነው።

የጉምዝዝ ጣፋጭ ነው
ባንዳፍታም ፉት አልነው
ለጥቀን ጨ...ለ...ጥ...ነ...ው።

አልኩኝ በሞቅታ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ቀጠለና ጓዴም ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ስንሸልል ፣ ስንፎልል ፣ ሳይገድረን እንቅልፍ
አንዳች ድምፅ ሰማን እሳት 'ሚያርከፈክፍ።

የሰደድ እሳቱ ዘንቦ ... ዘንቦ ... ዘንቦ!
ቡቃያውን መርጦ በቀይ ጎርፍ አጥቦ
የረገፈው ረግፎ ፣ የተረፈው ተርፎ
የደለል ሙላቱ አንጉዋሎ አንሳፎ
እኔም ተ--ን-ፌ ፣ ጓዴም ተ--ን-ፎ
ያለያየን መንገድ ባንድ ላይ ጠቅሎን
በስደት ታንኳ ላይ ዳግም አገናኘን።

ያ ጓዴና እኔ ፣ ዛሬም አልተማርን
ያ የቃል እባጩ ፣ ሶንኮፉ አልወጣልን
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
ንፈታችን ዉስጥ ... "እ-ና--ን-ፋ-ለ-ን!"
እያልን ዛሬም "አለን"።

ሐሙስ 3 ኤፕሪል 2014

የግጥም-ጥም

በምናብ መገለጥ ተጋግሮ
በብርሃን ሰይፍ ካልተቆረሰ፣

በፅናት መቀነት ጠብቆ
ባንጀት ካንጀት ካልተቋጠረ፣

በመራር ያሞት ከረጢት
በእውነት ካልተሰተረ፣

በሃሳብ እንዝርት ሹሮ
በስሜት ቀመር ተዳውሮ
በተቡ ቃላት ካልተሸመነ፣

በዉበት ጥለት ተቋጭቶ
በሕብረ-ቀለም ካልተሸለመ...

ካንገት በላይ ተጠምቆ
ቅራሪ ስንኝ ቢቀዳም፣
ምላስን ከማራስ አልፎ
የግጥምን ጥም አይቆርጥም።

ማክሰኞ 1 ኤፕሪል 2014

እነርሱ ለእርሱ

ያረገዝውን እያማጡ
ያማጠውን እየወለዱ
የወለደውን እየሳሙ
ያሳደገውን እየዳሩ
የሞተበትን እየቀበሩ
ሙት-አመት እየዘከሩ
በምስለ-እርሱ ሲኖሩ፣
እርሱ ሲፈልግ እርሱን
ስጋው ቢሸኛት ነፍሱን፣
ያልሆናቸው ግን የሆኑት
ጨክነው ሜዳ ላይ ሳይጥሉት፣
በእልፍ ፍራንክ በተገዛ
በተሰራ ከርጥብ ዋንዛ
በልኩ ጎጆ ቀለሱና
ያፈር ካባ ደረቡና
አስሸለቡት ላይል ቀና።

እሑድ 30 ማርች 2014

ተበልታ

 ተደግፋ ባጥንት
ተመርጋ በሥጋ
ተለስና በደም፣
እንቡጦቿን ቀጥፋ
ክፉ ዘመን አልፋ
ደብዛዋ ቢጠፋ፣
በየአደባባዩ ስፈልግ ስማስን
በደግ ሲነሳ ባጣው ሃያል ስሟን፣
በጨለመ ተስፋ ጥጋ-ጥጉን ሳስስ
እግር ጣለኝና ከምታቃስት ነፍስ፣
ደሟንም ተመጣ
ሥጋዋን ተግጣ
ተሰብሮ  አጥንቷ
መቅኔዋ ሲጠጣ፣
ባህያ ቆዳ ላይ ተንጋላ ተኝታ
አየኋት ሀገሬን በቀን ጅብ ተበልታ።

ሐሙስ 27 ማርች 2014

ያልዘራዉን ሊያጭድ

ጀግንነት ፣ ግብረገብ ፣ ሀገር ወዳድነት
ከዝና ባሻገር ፣ ለእሴት ኗሪነት
እብስ አሉ ጠፉ ፣ ተነኑ ባንድነት
ወኔ አልባ ሆኖ ፣ የቆረጠ ተስፋ
ሃሞቱ የፈሰሰ ፣ የተኛ ያንቀላፋ
ይለናል ያ ትውልድ
ያልዘራዉን ሊያጭድ።

በነፈዝነቱ ፣ እንዲህ እሚደቆሰው
ይህ የተኛ ትውልድ ፣ ማንስ ቀሰቀሰው?
ማንስ ምርኩዝ ሆኖ ፣ ማንስ ተነስ አለው?
ማንስ ከመማረር ፣ ማምረርን አሳየው?
ማንስ ከመልፈስፈስ ፣ ብርታት አስታጠቀው?
ማንስ የማይነትብ ፣ ፍሬ-ነገር ፃፈ?
ማንስ ሕያው ሥራ ፣ ትቶለት አለፈ?

በትናንት ልኬት እየተሰፈረ
'ሁሉም ድሮ ቀረ' እየተዘመረ
ያኔ ያልተዘራው ፣ ዛሬ ላይታጨድ
ላልሰመረው ሁሉ ፣ ይታማል ይህ ትውልድ።


እርቅ

ለይምሰል ለታይታ 
ስትለኝ ይቅርታ ፣ 
ሳይፈልቅ ከስሜትህ 
ከልብህ  ከውስጥህ ፣
ቂም ቋጥሮ ህሊናህ 
ቢጨብጠኝ እጅህ ፣ 
ብትስመኝ ብታቅፈኝ 
ያዞ እንባ እያነባህ፣ 
ከውስጥህ ተኳርፈህ ፣ ከኔ ከመታረቅ 
መጀመሪያ ነገር ፣ አንተ ካንተ ታረቅ።

ዓርብ 21 ማርች 2014

በእርግጥ ጎድተኸኛል

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
በናፍቆት ሰቀቀን
በመገፋት ቆፈን
እንደማለዳ ዉርጭ አኮራምተኸኛል።

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
ዱካህን አጥፍተህ በፈለግኩህ ጊዜ
ሰው አልባ አርገኸኝ ባገሬ በወንዜ
እንደቆላ ሃሩር አጠውልገኸኛል።

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
ሆነክ ያልሆንከዉን
ኖሮክ የሌለህን
ስትቃዥ በቁምህ
ክፉ ህልሜ ሆነህ እንቅልፌን ነጥቀሃል።

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
ዳብሰህ ሌላ ገላ
ጎርሰህ ሌላ ከንፈር
በቅናት ማዕበል አናውጠህ አዳፍተህ
ከሰው ተራ አውጥተህ
ከመሃል ዳር ገፍተህ
ከንፈሬን በጥርሴ አስነክሰኸኛል።

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
እቶን ወላፈኑ በሚንቦገቦገው
በበደል ምጣድ ላይ አገላብጠኸኛል
አሻሮ እስኪወጣኝ እስካ'ር ቆልተኸኛል ።

በእርግጥ ጎድተኸኛል፣
ዉስጤ  ግን ይልሃል......
ከበደል ከስቃይ ከበቀል ባሻገር
እጅ ባፍ እሚያስጭን የረቀቀ ሚስጥር
በልብ የሚዳሰስ ከስሜት ጥላ ስር
ማሪው ማሪው ይላል እውነተኛ ፍቅር።

ረቡዕ 19 ማርች 2014

ባህር ላይ ስራመድ

ዋናተኛው መንጋ
ሲንሳፈፍ ከታች ላይ፣
እኔ ግን ብቸኛው
ስራመድ ባህሩ ላይ፣
ለዚህ አይነት ጥበብ
አልደረሰም ብለው፣
ያዩትን ጥሬ ሀቅ
ወደጎን ትተው፣
ከቁብም ሳይቆጥሩኝ
አለፉኝ ናቅ አርገው።

እኔ ግን ብቸኛው
በሰፊው ባህር ላይ፣
ሲሻኝ ተቀምጬ
ኑሮን ሳሰላስል፣
ሲለኝ ተነስቼ
ስራመድ ያለእክል፣
ዋናተኛው መንጋ
ሰማሁት እንዲህ ሲል፣
"በዚህ በባህር ላይ ቆሞ 'ሚራመደው
እንደኛ ተንሳፎ መዋኘት ከብዶት ነው"።

ማክሰኞ 18 ማርች 2014

ባለጊዜ ታሪክ ጣፊ

የራሱን አሻራ ለማኖር ሲሳነው
የታሪክ ድሪቶ ሲጥፍ የሚዉለው
ባለ-ጊዜው ብእሩ ሀቅ እየደለዘ
የቆረቆረዉን ወቅጦ እየደቆሰ
የዛሬን መሰረት ትናንትን ናደና
መንደርኛ ጀብዱ አንቆ ጋተኝና
ያን የጋራ ቁስል
ያን የጋራ ገድል
ያን የጋራ ጀግና
በሰፈር ጉድጓድ ዉስጥ በጠበጠውና
ታሪክን አቡክቶ ጋገረበት መ'ና።

ሰኞ 17 ማርች 2014

መኖር

መኖር፣
ያለፈውን ፅልመት፣
ማህደሩን ዘግቶ።
መኖር፣
ባለው በቀረው ላይ፣
የተስፋ ዘር ዘርቶ።
መኖር፣
ከፊት ለሚመጣው፣
ቅን ልቦናን ከፍቶ።
አለበለዚያማ.......
ነገር-አለሙን ካከረርነው'ማ
ብንወጣት ብንወርዳት፣
ይህቺን ረቂቅ ዓለም
የጀመራት - ሁሉም፣
የጨረሳት - ማንም!

እሑድ 16 ማርች 2014

ሰው ለሰው

ለሰው መድሃኒቱ
ሰው ነው ቢሉኝ ጊዜ
ህመሜን ባዋየው
ቁስሌን ባሳየው
በፈውስ አስመስሎ ፣ ሸፍጥ ሰደደና
ስቃዬን አባሰው ፣ አስመረቀዘና።
......................እናም ተረዳሁኝ
የማዳኑን ያክል ፣ መድሃኒት በመሆን
ለሰው በሽታዉም ፣ ራሱ ሰው አንደሆን።

ረቡዕ 12 ማርች 2014

ያላወቅከው

እንደንጋት ጮራ፣
ከሚያበራው ፈገግታዬ
እንደበረዶ ነጥቶ፣
ከሚያስካካው ጥርሴ
እቅፍ ሳም አርገኝ፣
ከሚለው ገላዬ
.
.
.
ከዚህ ሁሉ ጀርባ መሽጎ
አንተን 'ሚታዘብህ ተሸሽጎ
የዋህነትህን 'ሚያይ አጮልቆ

እድሜ ዘመንህን ብትሰጠው
ተመራምረህ 'ማትጨብጠው
በልቤ ጓዳ የቋጠርኩት
አለ ያልገባህ ጠጣር እውነት
ስውር የታሪክ ጉንጉን ስፌት።

ወሊድ-አልባ ምጥ

መክኗል እንዳይባል ፣
የብሶት ምርጥ ዘር ፣ የኋሊት አዳቅሎ
በሕሊናው ማህፀን፣ ይዟል አንጠልጥሎ።

ጨንግፏል እንዳንል፣
ሌት ተቀን በማማጥ ፣ ሲቀመጥ ሲነሳ
ጭቆና ያጎበጠው ፣ አንድ ወገቡ ሳሳ።

አዋላጁም ሆኖ ፣ የሌለው እርባና
ምጡም ወሊድ-አልባ ፣ አስጨናቂ ሆነና
ሽሉን ተሸክመን ፣ ነግቶ እየጠባ  
የሚወለደውን ፣ ስንጠብቅ ባበባ
አፈር ላይ ያለነው አፈር እንዳንገባ።

ሰኞ 10 ማርች 2014

መንገዴን

ያመጣኝን መንገድ አርሰህ
'ምቹ' አስፋልት ስትጠርግልኝ፣
የኋሊት ምልከታ ስሻ
ገደል ከሆነ የሚታየኝ ፣
ሲሆን መንገዴን ጠግንልኝ
ካልቻልክ ጭራሽ አትንካብኝ።

ላቤ ወዙ

በብሶትህ ተረግዤ
በብሶትህ የተወለድኩ
ወኪልህ ነኝ ብሎ ፣
ሳልመርጠው ሳልፈቅደው
ወንበሩ ላይ ተደላድሎ፣
በኔ ላብ ይኖራል
ወዙ ጨፍ ብሎ።

ቅዳሜ 8 ማርች 2014

ዉሻና ሰው

ሰውና ዉሻማ ፣ ምን አንድ አድርጓቸው
ለሰው የማይዋጥ ፣ ልዩነት አላቸው።
የተራበ ዉሻ ፣ የጠገበ ለታ
ተመልሶ አይነክስም ፣ ያበላዉን ጌታ
የተራበ ሰው ግን ፣
የቀረበለትን ፣ አንድ ሁለቴ ጎርሶ
ደረቅ ጎሮሮውን ፣ በምፅዋት አርሶ
ጠኔ ያደከማት ፣ ነፍሱ መለስ ስትል
ይጎነጉነዋል ፣ የተንኮሉን ፈትል።

የስሜቴ አንባቢ


አንቺ የኔ አካል ፣ ሳትኖሪ ከጎኔ
መሰንበት ነው እንጂ ፣ መኖር አይደል የኔ
ከኔ ሐሴት ይልቅ ፣ ያንቺን እርካታ ላይ
አድማሱን አቋርጠሽ ፣ በሞቴ ቶሎ ነይ።

"ወድሻለሁ" ቃሉ ፣ ምን  ቢቀጭጭብኝ
ሳስቶ ሰዋ-ሰዉ ፣ ቅኔው ቢሰልብኝ
እንደበጋ ጅረት ፣ ቃላት ቢደርቁብኝ
እንደበቴ እንደሃረግ ፣ ቢጠላለፍብኝ
አንቺ ስላለሽኝ ፣ ብቻ እድለኛ ነኝ።

ለምን ቢባል ደግሞ ....................

ገፀ-ማንነቴን ፣ ግልጥልጥ አድርገሽ
የዉስጤን አስተዋይ ፣ አንባቢዬ አንቺ ነሽ።

ቅዳሜ 1 ማርች 2014

ሕይወት ማለት ወዳጄ

ሕይወት ማለት ፣
ሕይወት እኮ ሙዚቃ ናት ፣
በረቂቅ ቅኝት የምታዜማት
በዉብ ቅላፄ የምታስጌጣት ፣
ጉዳት ሲጨብጥህ ትተክዝባት ፣
ፍርሃት ሲከጅልህ ትፎክርባት ፣
ፌሽታ ሲነሽጥህ ትፈነጥዝባት።

አየህ ወዳጄ ፣
ሕይወት ማለት፣
ሕይወት እኮ ዉድድር ናት ፣
ህሊና በሚባል የራስ ዳኛ፣
በሕግጋት የምትመራ
መሸነፍ የሚሉት ፅልመት ፣
ማሸነፍ የሚባል ንጋት ፣
በፈረቃ የሚያደምቋት
ወጪ ወራጁን እምታሳይ ፣
የፍትጊያ አውድማ ናት።

እና ወዳጄ ፣
ሕይወት ማለት ፣
ሕይወት እኮ መስዋዕትነት ናት ፣
እንዳሻህ በብላሽ ፣ ከየትም የማታፍሳት
ወገብህን ሸብ ጠበቅ አርገህ ፣
ጥፍርህ አስኪቆስል ዳገት ቧጠህ ፣
ወደ ማምሻው ነው የምትቆናጠጣት።

ስማኝማ ወዳጄ ፣
ሕይወት ማለት ፣
ሕይወት እኮ ቅኔ ናት ፣
ያለ ጠብ-መንጃ ዘርፈህ ፣
በቀለጠው ሰሟ ተውልዉለህ ፣
በነጠረው ወርቋ ትደምቅባት።

ከምንም በላይ ወዳጄ ፣
ሕይወት ማለት ፣
ሕይወት እኮ ፍቅር ናት ፣
በቁሳቁስ ቅራቅንቦ ፣ በንዋይ የማትለካት ፣
ሳትሰጥ ተቀብለህ ፣ ሳትቀበል የምትሰጣት።

(የበድሉ ዋቅጅራን  "ሀገር ማለት የኔ ልጅ" በማሰብ የተፃፈ)

ረቡዕ 19 ፌብሩዋሪ 2014

ካንቺ ጋራ

ደማቅ ከዋክብት ፣ ከልባቸው እየሳቁ
እኔና እንቺን ብቻ ፣ በደስታ ሲያጠምቁ
ጨረቃዋም ፣ ፈክታ በተራዋ
ስታስጌጠን ፣ በጣፋጭ ፈገግታዋ
በፍቅርሽ ምትሃት ፣ ተዘውሬ
ብቅ እላለሁ ፣ እንደገና ተፈጥሬ።

አንድም ቃል ፣ ካንደበታችን ስይወጣ
ጮክ ብለን ስናወጋ ፣ ፍፁም በፀጥታ
ፈውሰ-ፍቅርሽ ፣ በደሜ ናኝቶ
ህመም መከራዬን አሰናብቶ
የጊዜ ዑደት፣ ሕጉ ላልቶ
ያሳለፍናቸው ፣ እልፍ ቀናት
ያጥሩብኛል ፣ እንደ ቅፅበት
አይን ጨፍኖ ፣ እንደመክፈት።



ያላዋቂ ታዋቂዎች

አዋቂ አስተዋዮች፣
መተንፈስ ሲከለከሉ
ወይ ስጠፈነጉ ፣
ወይ ሲገፉ እስኪወድቁ

ያላዋቂ ታዋቂዎች፣
በሚያነሱት የሐሰት አቧራ
የማስተዋል ጉንፋን ያዘን፣
ማስነጠሱ የማያባራ

ያላዋቂነታቸው ግዝፈቱ፣
እንደ ህዋ ስፋቱ
እንደ ዉቅያኖስ ጥልቀቱ

ሲገላበጥ መዝገበ-ቃላታቸው፣
ሆድ እንጂ ህሊና አያስነብባቸው

የመጣዉን መስሎ አዳሪ ፣
ለማሽቃበጥ ፊታውራሪ ፣
ሆድ ለመሙላት ብቻ ኗሪ

ለተንሸዋረረው አይነ-ህሊናቸው፣
የትዉስት ነው መነፅራቸው ፣
አሱም አርቆ አያሳያቸው

አለማወቃቸዉን ባለማወቃቸው
ትዉልድ ይሻገራል ድንቁርናቸው።